Friday 5 December 2014

Joshua Breakthrough Renewal Teaching and Preaching Ministry ክፍል አራት



ክፍል አራት

ይህ Joshua Breakthrough Renewal Teaching and 
Preaching Ministry
አገልግሎት ሥር እየተዘጋጀ የሚቀርብላችሁ መንፈሳዊ ትምህርት ነው
ዛሬ ደግሞ የምንማማርበት ሃሳብ ካለፈው ከክፍል ሦስት ትምህርት የቀጠለ ሆኖ ይሄ ኢየሱስ በሰማያት ያለፈ ትልቅ ሊቀ ካህናት በመሆኑ ምሕረትንና ለእርዳታም ጸጋን የሚሰጥ መሆኑን ለማስተማር ነው ኢየሱስ ሊቀካህናት ሆኖ በሥጋው ወራት በምድር በተመላለሰበት ጊዜ የሰው ልጆችን ኃጢአት ያስተሠርይላቸው ነበር ምሕረትንም ይሰጣቸው ነበር ከእርሱም ሌላ ኃጢአትን ሊያስተሠርይ የሚችል ምሕረትንም ሊሰጥ የሚችል እንደሌለ በክፍል ሦስት ትምህርታችን ላይ በሰፊው ከእግዚአብሔር ቃል ማስረጃ በመስጠት እንደገናም ቤተክርስቲያኒቱ ከምትጠቀምባቸው መጻሕፍት መካከል ይህንኑ እውነት የሚደግፉ አንዳንድ እውነቶችን አንስተን በተገቢው መንገድ አብራርቻለሁ ነገር ግን አሁንም ይህ ሃሳብ በደንብ ያልገባቸው ሰዎችና ቢገባቸውም መረዳታቸውን መልቀቅ ሽንፈት የሚመስላቸው ሰዎች መጽሐፍቅዱሳችንና እነዚህም የኦርቶዶክስ መጻሕፍት የሚደግፉአቸውን የኢየሱስን በምድር በነበረ ጊዜ በሊቀካህንነቱ የሠራቸውን ሥራዎች የሰጣቸውን የኃጢአት ሥርየት እና ብዙ የሆነን ምሕረት በመካድና በማስተባበል ራስህን ለካህን አሳይ ብሎአል ኢየሱስ የምትለዋን ጥቅስ ብቻ መዘዝ አድርጎ በማውጣት ዛሬም ኃጢአትን የሚያናዝዙ ይቅርም የሚሉ ካህናትና ነፍስ አባት እንዳሉ ሊያሳዩን ሞክረዋል መጽሐፉ ግን እንደዚህ አያስተምረንም በዚያን ዘመን ኃጢአትን የሚያናዝዙ ይቅርም የሚሉና ምሕረትን የሚሰጡ ካህናት ቢኖሩ ኖሮ ኢየሱስ እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ ወደ እኔ በማለት ሰዎችን ከኃጢአት ሸክም ሊያሳርፍ ይህን የመሰለ የተባረከ ጥሪ አያደርግም እንደገናም ኃጢአትሕ ኃጢአትሽ ተሠረየልህ(ልሽ) ብሎ ሕዝቡን በሰላም አያሰናብትም ነበር ይልቁንም ይህንን ሁሉ ሊያደርጉ ለሚችሉ በጊዜው ለነበሩ ካህናት ይህንኑ ከኃጢአት ሸክም የማሳረፉን ሥራ ኃጢአትንም ይቅር የማለቱንና ምሕረትም የመስጠቱን ሥራ ለእነዚሁ ካህናት ይተውላቸው ነበር ነገር ግን በዚያን ዘመን የነበሩ የብሉይ ኪዳን ካህናትም ሆኑ ዛሬ ላይ አለን ማናዘዝና ይቅር ማለት ምሕረትም መስጠት እንችላለን የሚሉ ካህናት ይህንን ለማድረግ በፍጹም የማይችሉ በመሆናቸውና  እናድርግ ቢሉም ሥልጣኑም ሆነ መብቱም የሌላቸው በመሆኑ ኢየሱስ ይህንን ሊያደርግ መጣ እንደውም ኢየሱስ የመጣበት ዋናውና መሠረታዊ የሆነ ዓላማውም ኃጢአትን ይቅር ማለትና ምሕረትንም  ለሰው ልጆች መስጠት ነው ከዚህ ጌታ ውጪ ኃጢአትን ይቅር የሚል ምሕረትንም የሚሰጥ ማንም የለም እግራችን እስኪነቃ ድረስ ብንፈልግም አናገኝም ስለዚህ ከቃሉ ውጪ የሆነውን ትክክለኛ መረዳት የሌለበትን አሮጌ አስተሳሰብ ወዲያ ጥለን ከተጻፈልን ቃል ጋር እና የመጀመርያዎቹ የቤተክርስቲያን አባቶችም ኢየሱስ ክርስቶስ እስመ አበ ነፍስየ አንተ በማለት ኢየሱስ እውነተኛው የነፍስ አባታችን ሆኖ ኃጢአታችንንም አናዞ ይቅር የሚለን ታማኝ የነፍስ አባታችን መሆኑን ገልጽውልናል ካህናቱም በሠርዎተ ሕዝብ ማለትም ሕዝብን በሚያሰናብቱበት ጊዜ የካህናት አለቃ ኃጢአትን የሚያስተሠርይ ይቅር ባይ እያሉ ነውና የጸለዩት የኢየሱስ ክርስቶስ ሊቀካህናትነትና ኃጢአትንም ይቅር ማለት አምነን ልንቀበል ይገባል እንደገናም ይህ እውነት በትክክል እና  በብዙ በማስረጃም የተጻፈልን በመሆኑ ከቶውንም ቢሆን የሚያደናግረን አይሆንም ወገኖች እንግዲህ ከነዚህና ከዚህ በፊትም ከተጻፉልን እውነቶች አኳያ  የኢየሱስን ሊቀካህናትነት ተቀብለን ለኢየሱስ ብቻ ኃጢአታችንን መናዘዝ ሸክማችንንም ለእርሱ መስጠት ይኖርብናል ያኔ ኢየሱስ በደሙ ያጥበናል ኃጢአታችንን ይቅር ሊለን ከዓመጻም ሁሉ ሊያነጻን የታመነ ፣ ጻድቅም ነውና ኃጢአታችንን ይቅር ይለናል ከዓመጻም ሁሉ ያነጻናል 1 ዮሐንስ 1 7 _ 10  ኢየሱስ በሰማያት ያለፈ ሊቀካህናት በመሆኑም ምሕረትንና ለእርዳታም ጸጋን የሚሰጥ ነው ዕብራውያን 4 16 መቼም ምሕረትን የሚጠላ ለደከመ ሕይወቱም ብርታትን ለማግኘት ጸጋን የማይፈልግ ማንም የለም እኔ ብርቱ ነኝና ምንም አያስፈልገኝም ያለ ሰው ካለ ወደዚህ ወደ ጸጋ ዙፋን አለመቅረብ ደግሞ መብቱ ነው ነገር ግን አንድ የምናገረው እውነት ማንም ኃጢአት የሌለበት ምሕረትም የማያስፈልገው እንደገናም  ከድካሙ ለመውጣት ሲል ጸጋን ከእግዚአብሔር የማይለምን ጸጋም የማያስፈልገው ማንም ብርቱ ሰው የለም ስለዚህ ምሕረት የሚፈልግ አዲስ ጌታን የማያውቅና ጌታንም እንደ ግል አዳኙ አድርጎ ያልተቀበለ ሰው ብቻ ሳይሆን ጌታንም አውቆ ከሥጋው ድካም የተነሳ የበደለና ኃጢአትንም ያደረገ  ምሕረትን ለማግኘት የሚቀርበው ወደዚህ ወደ ጸጋው ዙፋን ነው ይሄ የጸጋ ዙፋን የጸጋ ዙፋን የተባለበት ምክንያት በክርስቶስ ኢየሱስ ሞትና ትንሣኤ በተደረገው ብቸኛ የሰው ልጆች መዳን ሰዎች ጌታ ኢየሱስን እንደ ግል አዳኛቸው አድርገው ተቀብለው ለመዳን የሚቀርቡበት ብቸኛው መንገድ ስለሆነ ነው ሮሜ 4 24 እና 25  ለመዳንም በዚሁ የጸጋው ዙፋን ሥር ወስነው ንስሐ ሲገቡና ጌታ ኢየሱስንም እንደ ግል አዳኛቸው አድርገው ሲቀበሉ ዙፋኑ የጸጋ ዙፋን ነውና እግዚአብሔር በምሕረት ልጆቹ አድርጎ ይቀበላቸዋል የዮሐንስ ወንጌል 1 12 እና 13 ጌታን ተቀብለውና አዲስ ፍጥረት ሆነው የበደሉ ጥፋትንም ያደረጉ ሲገኙ ደግሞ  እግዚአብሔር ልጆቹን አሁንም በምሕረት ይቀበላል ለዚህ ነው ዳዊት እኔ ግን በምሕረትሕ ብዛት ወደ ቤትሕ እገባለሁ አንተን በመፍራት ወደ ቅድስናህ መቅደስ እሰግዳለሁ ያለው መዝሙር 5 7 ነቢዩ ኤርምያስም በሰቆቃው መጽሐፉ ላይ ያልጠፋነው ከእግዚአብሔር ምሕረት የተነሣ ነው ርኅራኄው አያልቅምና ማለዳ ማለዳ አዲስ ነው ታማኝነትሕ ብዙ ነው አለ ሰቆቃወ ኤርምያስ 3 22 እና 23 የጠፋውን ልጅና ገንዘቡንም ከአመንዝሮች ጋር የጨረሰውንም ልጅ ታሪክ ብንመለከት አባቱ የተቀበለው በምሕረት ነው የሉቃስ ወንጌል 15 11 _ ፍጻሜ እግዚአብሔር አንድ ጊዜ ብቻ ሳይሆን ሁልጊዜም በምሕረቱ ይቀበለናል ዛሬም ያለነውና የምንኖረው በእግዚአብሔር ምሕረት ነው  እንደገናም ጸጋን ለአማኞች መስጠትን በተመለከተ በሚያስፈልገን ጊዜ የሚረዳንን ጸጋ እንድናገኝ ወደ ጸጋው ዙፋን በእምነት እንቅረብ ስለሚል ቃሉ በሰማያት ያለፈው ሊቀካህናችን ኢየሱስ የሚያስፈልገንን ጸጋ ይሰጠናል ለዚህ ነው  ጳውሎስን ጸጋዬ ይበቃሃል ሃይሌ በድካምህ ይገለጣል ያለው የመጽሐፉን ክፍል ሄደን ስንመለከት እንዲህ ይላል ስለዚህም በመገለጥ ታላቅነት እንዳልታበይ የሥጋዬ መውጊያ፥ እርሱም የሚጎስመኝ የሰይጣን መልእክተኛ ተሰጠኝ፤ ይኸውም እንዳልታበይ ነው ስለዚህ ነገር ከእኔ እንዲለይ ሦስት ጊዜ ጌታን ለመንሁ እርሱም፦ ጸጋዬ ይበቃሃል፥ ኃይሌ በድካም ይፈጸማልና አለኝ ይለናል 2 ቆሮንቶስ 12 7 _ 9 እናንብብ እንግዲህ ጌታችን ኢየሱስ ጸጋን የማይሰጥ ቢሆን ኖሮ ጸጋዬ ይበቃሃል ባላለውም ነበር ጸጋን መስጠትን በተመለከተ ከመጽሐፍቅዱሳችን ብዙ ክፍሎችን አውጥተን መመልከት እንችላለን ለአሁን ግን ለትምህርታችን ማስረጃ እንዲሆን ይሄ ይበቃናል ያልዳንን ጌታንም እንደ ግል አዳኛን አድርገን ያልተቀበልን ሰዎች የምንድነው ጌታን የሕይወታችን ጌታና አዳኝ አድርገን በመቀበል በጌታ ምሕረት ነው ምክንያቱም መጽሐፍ ሲናገር እንግዲህ ምሕረት ለወደደ ወይም ለሮጠ አይደለም፥ ከሚምር ከእግዚአብሔር ነው እንጂ ይለናል ሮሜ 9 16 ስለዚህ ምሕረትን አግኝቶ የእግዚአብሔር ልጅ ለመባልና የመንግሥቱም ወራሽ ለመሆን ወዲያና ወዲህ ሳይሉ የራስንም አማራጭ የሆነ የመዳኛ መንገድ ሳያዘጋጁ አዘጋጅተውም ከሆነ እነዚያኑ መንገዶች በጊዜ በመተው  የመዳን ቀን አሁን ነውና ጊዜ ሳያጠፉ በቀጥታ ወደ ጸጋው ዙፋን መጥቶ በጸጋው ዙፋን ሥር በእውነተኛ ንስሐ በመውደቅ በክርስቶስ አማካኝነት ከማረንና ሙሉ የሆነውን ምሕረቱንም ከሰጠን ከእግዚአብሔር ምሕረትን መቀበል ነው በክርስቶስ የተገኘውን የእግዚአብሔርን ምሕረት በተመለከተ መጽሐፍቅዱሳችን እጅግ አስደናቂ የሆነ እውነት ይናገራል ወይስ ዓመፀኞች የእግዚአብሔርን መንግሥት እንዳይወርሱ አታውቁምን ? አትሳቱ፤ ሴሰኞች ቢሆን ወይም ጣዖትን የሚያመልኩ ወይም አመንዝሮች ወይም ቀላጮች ወይም ከወንድ ጋር ዝሙት የሚሠሩ ወይም ሌቦች ወይም ገንዘብን የሚመኙ ወይም ሰካሮች ወይም ተሳዳቢዎች ወይም ነጣቂዎች የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም ከእናንተም አንዳንዶቹ እንደ እነዚህ ነበራችሁ፤ ነገር ግን በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም በአምላካችንም መንፈስ ታጥባችኋል፥ ተቀድሳችኋል፥ ጸድቃችኋል አለን 1ኛ ቆሮንቶስ 6 9 _ 11 መቼም ለአንዳንዶቻችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም በአምላካችንም መንፈስ ታጥቤ ተቀድሻለሁ ጸድቄያለሁ የሚለውን ቃል አምኖ ለመቀበልና ተቀድሻለሁ ጸድቄያለሁ ለማለት ቢከብድም መጽሐፉ በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም በአምላካችሁ መንፈስ ታጥባችኋል ተቀድሳችኋል ጸድቃችችኋል ይለናልና ታጥበናል ተቀድሰናል ጸድቀናል ስለዚህ ዛሬ ባጠበን በቀደሰንና ባጸደቀን በዚሁ ጌታ ያመንን ቅዱሳን ወገኖች ወደፊትም የምናምን ሕዝቦችና ልናምንም የተዘጋጀን ሰዎች ካለን ወደዚሁ እውነት በመምጣት ጌታንም በመቀበል ስማችንን እገሌ እና እገሊት በሚለው ቦታ በማስገባት ቅዱስ እገሌ ጻድቅ እገሌ ቅድስት እገሌ ጻድቅት እገሌ ተብለን ልንጠራ የተገባን ሆነናል አንዳንዶች ግን ይህን እውነት በውል ሳይረዱ ቅዱስና ጻድቅ ያሰኘንንም ጌታ ሳያውቁ እናንተም ብሎ ጻድቅ ? እናንተም ብሎ ቅዱስ ? ጻድቅና ቅዱስ ነን ስትሉ ትንሽ እንኳ አታፍሩም እንዴ ? ብለው ጥያቄ ያቀርቡልናል ሊሟገቱንም ይጥራሉ  እነርሱ ጻድቅና ቅዱስ ብለው ከጻድቃንና ከቅዱሳን ጎራ የመደቧቸው ጻድቅና ቅዱስ ሊሆኑ በራሳቸው ኃይል ደንና ዱር ውስጥ ገብተው የዱር ፍራፍሬ የሚበሉትን ቅጠል ያገለደሙትን ገደል ውስጥ ተሸሽገው የሚኖሩትን ነው መጽሐፍቅዱስ  የሚነግረን ጽድቅ ግን እግዚአብሔር በክርስቶስ በኩል ያዘጋጀውን የጽድቅ መንገድ ነው ስለዚህም ነው ወይስ ዓመፀኞች የእግዚአብሔርን መንግሥት እንዳይወርሱ አታውቁምን ? አትሳቱ፤ ሴሰኞች ቢሆን ወይም ጣዖትን የሚያመልኩ ወይም አመንዝሮች ወይም ቀላጮች ወይም ከወንድ ጋር ዝሙት የሚሠሩ ወይም ሌቦች ወይም ገንዘብን የሚመኙ ወይም ሰካሮች ወይም ተሳዳቢዎች ወይም ነጣቂዎች የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም ከእናንተም አንዳንዶቹ እንደ እነዚህ ነበራችሁ፤ ነገር ግን በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም በአምላካችንም መንፈስ ታጥባችኋል፥ ተቀድሳችኋል፥ ጸድቃችኋል በሚል በእግዚአብሔር ቃል የተጻፈልን እኛ በራሳችን እራሳችንን ልናጸድቅና ቅዱስ ልናሰኝ ገዳም ብንገባ ዱር ውስጥ ብንወድቅ ለቁመተ ሥጋ ብቻ ብለን የጣፈጠም ምግብ ሳንበላ ፍራፍሬ ለመብላት  ብንገደድ እንደገናም ከዚህ ሌላ ልዩ ልዩ ሆነን የመጽደቅያ ቅዱስ የመሆኛም መንገድ ብናዘጋጅ  እግዚአብሔር ግን አሁንም የሚያውቀን በአመጸኝነታችን ነው ምክንያቱም የሮሜ መጽሐፍ ጻድቅ የለም አንድ ስንኳ አስተዋይም የለም እግዚአብሔርንም የሚፈልግ የለም ሁሉ ተሳስተዋል በአንድነትም የማይጠቅሙ ሆነዋል እያለ ይናገራል ወረድ ብሎ ደግሞ አፍም ሁሉ ይዘጋ ዘንድ ዓለምም ሁሉ ከእግዚአብሔር ፍርድ በታች ይሆን ዘንድ ሕግ የሚናገረው ሁሉ ከሕግ በታች ላሉት እንዲናገር እናውቃለን ይህም የሕግን ሥራ በመሥራት ሥጋ የለበሰ ሁሉ በእርሱ ፊት ስለማይጸድቅ ነው፤ ኃጢአት በሕግ ይታወቃልና አለን ሮሜ 3 11 _ 25 ስለዚህ ጻድቅ ካልሆነ ሰው አስተዋይ ካልሆነና ከተሳሳተ ሰው አፉም ይዘጋ ዘንድ ከፍርድ በታች ከሆነ ሰው የእግዚአብሔር ፍርድ እንጂ ጽድቅ አይጠበቅም ለዚህ ነው መጽሐፍ ቅዱስ የሆነውን ነገር በመንገር ነገር  ግን ብሎ ይጀምርና  በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም በአምላካችንም መንፈስ ታጥባችኋል፥ ተቀድሳችኋል፥ ጸድቃችኋል የሚለን  የወንጌሉ እውነት የሚነግረን እንግዲህ ይህንን ነው ስለዚህ ያልታጠብን ያልተቀደስን እና ያልጸደቅን ሰዎች ሌላ መታጠብያ  መጽደቅያና መቀደሻ መንገድ ከምናዘጋጅ ይልቅ የእኛን ነገር ሳይጠብቅ ከዘላለማዊ ፍቅሩ የተነሳ እንዲሁ በሞቱ በከፈለልን ዋጋ በደሙ ባጠበን ባጸደቀን በቀደሰን ጌታ አሁኑኑ አምነን መታጠብ መጽደቅና መቀደስ ይሁንልን ነገር ግን ለመዳን መቅረብያ የሆነ የጸጋ ዙፋን  አግኝተን በዚህ ዕድል የማንጠቀም ከሆነ ይሄ የጸጋ ዙፋን የጸጋ ዙፋን መሆኑ ቀርቶ  ለፍርድ ብቻ የሚሆን ዙፋን ይሆናል ያን ጊዜ ምን እንደምንሆን አላውቅም በመሆኑም በዕድሜያችን ሳንጫወትና ሞትም ሳይቀድመን ዛሬውኑ የሚያዛልቀንን መያዙ ለእኛ መልካም ነው መጽሐፉ ኢየሱስን በሰማያት ያለፈ ትልቅ ሊቀ ካህን እያለው ኢየሱስ ሊቃካህናታችን አማላጃችን ሳይሆን ፈራጃችን ነው ማለቱ አለማወቅ በመሆኑ ትልቅ መታወርና አውጣኪነትም ነው የጥንቷ ሐዋርያዊትና ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን አውጣኪን የለየችው ኢየሱስ ክርስቶስ ከተነሣና ካረገ በኋላ መለኮት ሙሉ ለሙሉ ሥጋን የዋጠውና ያጠፋው በመሆኑ በሰማይ የሆነውን የሰውነቱን ሥራ አናየውም በሰውነቱም በአብ ቀኝ አልተቀመጠም በማለቱ ቤተክርስቲያኗ ይህንኑ አውቃ ከስህተቱ እንዲመለስ ብዙ ከመከረችው በኋላ ከነትምህርቱ ለይታዋለች ታድያ ዛሬም ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን አሸንፎ ወደ ሰማይ በመውጣቱ አምላክ ነውና ፈራጅ ነው እንጂ አማላጅ አይደለም ማለቱ አውጣኪነት ነው ያልኩት ለዚህ ነው ኢየሱስ ወደ ሰማይ ቢወጣም በአምላክነቱ ብቻ ሳይሆን በሰውነቱም ጭምር ነው ሙሉው የጥንቷ ቤተክርስቲያን ጤናማ ትምህርት ይሄ ነው ክርስቶስ ሞትን አሸንፎ በአምላክነቱ ብቻ ሳይሆን በሰውነቱም ጭምር ወደ ሰማይ መውጣቱ  ለዚህ ነው በዮሐንስ ወንጌል 3 13 ላይ ወአልቦ ዘዐርገ ውስተ ሰማይ ዘእንበለ ዘወረደ እምሰማይ ወልደ እጓለ እመሕያው ዘውእቱ ይነብር ውስተ ሰማይ ያለው ወደ አማርኛው ስንተረጉመው ከሰማይም ከወረደ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ ማንም የለም፥ እርሱም በሰማይ የሚኖረው የሰው ልጅ ነው የሚል ትርጉምን የሚሰጥ ነው ስለዚህ ኢየሱስ ወደ ሰማይ ከመውጣቱም ባሻገር የእግዚአብሔር ልጅ ብቻ ሳይሆን የሰውም ልጅ ሆኖ በሰማይ የሚኖር ነው በመስቀሉ ወራት የሕዝብ ሽማግሌዎችና የካህናት አለቆች ተሰብስበው ክርስቶስን ወደ ሸንጎ ወስደው ንገረን አንተ ክርስቶስ ነህን ? ብለው በጠየቁት ጊዜ የሰጠው መልስ አስደናቂ ነበር እርሱ ግን እንዲህ አላቸው፦ ብነግራችሁ አታምኑም ብጠይቅም አትመልሱልኝም አትፈቱኝምም ነገር ግን ከአሁን ጀምሮ የሰው ልጅ በእግዚአብሔር ኃይል ቀኝ ይቀመጣል አላቸው ሁላቸውም እንግዲያስ አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህን ? አሉት  እርሱም፦ እኔ እንደ ሆንሁ እናንተ ትላላችሁ አላቸው እርሱም፦ ራሳችን ከአፉ ሰምተናልና ከእንግዲህ ወዲህ ምን ምስክር ያስፈልገናል ?  አሉ ይለናል የሉቃስ ወንጌል 22 66 _ 71 ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ ብቻ ሳይሆን የሰውም ልጅ መሆኑን አምኖ ነገር ግን ከአሁን ጀምሮ የሰው ልጅ በእግዚአብሔር ኃይል ቀኝ ይቀመጣል ሲላቸው እነርሱ ደግሞ የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን ተጠራጥረው እንግዲያስ አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህን ?  ሲሉ ጥያቄ አቀረቡለት በዚህም ኢየሱስ የሰጠው መልስ ግን አጥጋቢ ነበር ታድያ ዛሬም በዘመናችን ወንጌል የሚለው ምን እንደሆነ ሳያውቅ አንብቦም ሳይረዳ ሳይማር በሰኔ ጐልጎታና በራዕየ ማርያም ሰው ሰራሽ ድርሰቶችና ልብ ወለዶች አስተሳሰቡ የታወራው አንዳንዱ ትውልድ ደግሞ ጭፍን በሆነ መረዳቱ ሊያስተባልል ሊክድም የሚሞክረው እንደ አይሁድ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን ሳይሆን የሰውም ልጅ ሆኖ በእግዚአብሔር ኃይል ቀኝ መቀመጡን ነው እኛም ታድያ ወንጌል አልገባ ብሎት በሰኔ ጐልጎታና በመሣሠሉት ተረቶች ታስሮ በታወረ አዕምሮ ኢየሱስ የሰው ልጅም ሆኖ በእግዚአብሔር ቀኝ መቀመጡን ሊክድ ቢሞክርም እንደዚያ ሊቀካህን ልብሱን ቀዶ እስኪያብድ ይድረስ እንጂ ይህ ክርስቶስ የሰው ልጅም ሆኖ በእግዚአብሔር ቀኝ የተቀመጠ መሆኑን በይፋ እንናገራለን የማርቆስ ወንጌል 14 50 _ 65 ታድያ ብዙዎችን እንደተረዳኋቸው ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ ሆኖ ብቻ ሳይሆን የሰው ልጅም ሆኖ በእግዚአብሔር ቀኝ መቀመጡን ለመናገር የማይደፍሩበት ትልቁ ምክንያት ሊቀ ካህናትና አማላጅ ነው የሚለውን እውነት ከመፍራትና ከመሸሽ የተነሳ ነው ክርስቶስ በሰውነቱ በአብ ቀኝ የተቀመጠው ደግሞ እንዲሁ መቀመጥ ስላስፈለገው ሳይሆን እኛን የሰው ልጆችን ከአብ ጋር ለማስታረቅና ለማማለድ ነው ስለዚህ ይሄን በማማለድ አገልግሎት በሥራ ላይ ያለውን ጌታ አማላጅ አይደለም ፈራጅ ነው ማለት የማማለዱን ሥራ ማስተባበልና መካድም በመሆኑ ትልቅ ድንቁርና ነው እንላለን ኢየሱስ በሰማይም ሆኖ በሥራ ላይ ያለ አማላጅ ለመሆኑ የቤተክርስቲያኒቱ የሰዓታት መጽሐፍ አብ በእንተ ኢየሱስ ርድአነ ክርስቶስ ኃበ አቡከ ሄር አማህጸነነ መንፈሰ አብ ወወልድ ናዝዘነ  በማለት አብ ሆይ ስለ ኢየሱስ ብለህ እርዳን ክርስቶስ ሆይ ወደ ቸሩ አባትህ አማልደን የአብና የወልድ መንፈስ ሆይ ቃትትልን ጸልይልን እያለ ሲናገር እንመለከታለን እንደገናም በዚሁ የሰዓታት መጽሐፍ ላይ ሊቀ ካህናት ዘይቀውም ሎሙ ለቅዱሳን በደብተራ ስም እንተ እግዚአብሔር ተከላ ውእቱ ኢየሱስ ክርስቶስ ይለናል እግዚአብሔር በተከላት ድንኳን ለቅዱሳን የሚቆም ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ ነው ማለቱ ነው እግዚአብሔር የተከላት ድንኳን በምድር ያለች የሰለሞን ቤተመቅደስ አይደለችም ወደዚያማ የበግና የፍየል ኮርማ ይዘው ብዙዎች የብሉይ ኪዳን ሊቃነ ካህናት ገብተውል ቢገቡም ግን ከአብ ጋር ሊያስታርቁን አልቻሉም ለአንዴና ለዘላለም ከአብ ጋር ሊያስታርቀን በእጅ ወደ አልተሠራች ወደዚች ድንኳን ኢየሱስ ቀዳሚ ሆኖ ገባልን ዕብራውያን 6 17 _ 20 ዕብራውያን 9 11 _ 14   23 _ 28 ታድያ ይህንን የመሠለ የእግዚአብሔር እውነት ይዛ በተዋቡ ዜማዎችዋ በሌሊት ሊቀካህናት ዘይቀውም ሎሙ ለቅዱሳን እያለች የምታዜመዋ ቤተክርስቲያን እንደገና ወደ ኋላ ተመልሳ የሰሎሞን ቤተመቅደስን በመስራትና መስዋዕት አቅራቢዎች ካህናትን በመሾም ሥጋ እና ደሙ እያለች መስዋዕት ማቅረቧ በሌሊት በሰዓታት መጽሐፏ ላይ የምትዘምረውና በጠዋት በሰሎሞን በተመቅደስዋ ውስጥ ገብታ የምታካሂደው የቅዳሴ መሥዋዕትና የክህነት አገልግሎት በእጅጉ የሚቃረን በመሆኑ ቤተክርስቲያኒቱን አላዋቂ አድርጎ ግምት ውስጥ የጣላት ስለሆነ በጣም የምታሳዝን ሆናለች እንደገናም ያለማዕረጋቸው ማዕረግ ያለቦታቸው ሹመት ስጣታ በሥራ ላይ ያሰማራቻቸው እነ ሊቀ ጠበብት ዶክተር ዘሪሁን ሙላቱ ኦርቶዶክስ መልስ አላት ለሚለው ትምህርታቸው ሀሞን ጎግ በሚለው ቪሲዲያቸው የሰጡትን መልስ ሰምተን ከሊቀጠበብትነታቸውና ከዶክተርነታቸው ይልቅ አላዋቂነታቸው እጅግ ጎልቶና ሰፍቶ በማየታችን ይህንን ሁሉ እላያቸው ላይ ያላቅማቸው የቆለሉትን ሥልጣን በጊዜ ቁጭ አድርገውና አስቀምጠው ወደ መጽሐፍቅዱስ ትምህርት ቤት ቢገቡ አለበለዚያም ከእነዚህ መልስ ሰጠኋቸው ብለው ከተከራከርዋቸው ሰዎች እግር ሥር ቁጭ ብለው በረጋ መንፈስና በጥሞና ቢማሩ አሁን ላይ ደርሼበታለሁ ይዤውማለሁ ብለው አፋቸውን ሞልተው ቤተክርስቲያኒቱንም ወክለው ለሚናገሩበት ሥልጣን ማለት ለሊቀጠበብትነቱና ለዶክተርነቱ ብቁ ይሆናሉ ብዬ አስባለሁ አሁን ግን ብቁ ነኝ ብለው ቤተ ክርስቲያንንም ወክለው አፋቸውን ሞልተው የተናገሩ ቢሆኑም  የሰጡት መልስ  ግን እንኳን ቤተክርስቲያንን ሊወክል  አንድን እውነተኛ የኦርቶዶክስን አማኝ የማይወክል በመሆኑ በጣም አሳዝኖናል በኢየሱስ አማላጅነት እና አስታራቂነት ጉዳይ ኦሮቶዶክስ መልስ አላት ኢየሱስ አማላጅና አስታራቂ አይደለም ኢየሱስ ፈራጅ ነው ብለዋል እኛ ደግሞ እንዲህ እንላለን እርሳቸው እንዳሉት በዚህ የኢየሱስ አማላጅነት እና አስታራቂነት ጉዳይ የጥንቷና የመጀመርያዋ ኦርቶዶክስ ከሆነ ልክ ነው መልስ አላት መልሱንም ይኸው አቅርቤዋለሁ አዎን ኢየሱስ አማላጅ ነው አስታራቂ ነው ትላለች ጥንታዊቷ ሐዋርያዊትዋና ዓለማቀፋዊቷ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን አማላጅነቱንና አስታራቂነቱን ክዳ ግን በደፈናው በጭፍንነትና ባልተረዳ ማንነት ሊቀጠበብት ዘሪሁን እንዳሉት ኢየሱስ ፈራጅ ነው አትልም ይህ ከእውነት የራቀ ውሸት ነው ስለዚህ ሊቀጠበብት ዘሪሁን ይህንን እውነት ተረድተው በፍጥነት ከስሕተታቸው እንዲታረሙ በትሕትና እጠይቃቸዋለሁ ለዚህም ነው ያለጊዜያቸው ማዕረግ ወስደውና ሊቀጠበብት ዘሪሁን ተብለው መድረክ ላይ እውቀት በጎደለው አነጋገር መልስ ሊሰጡ ደፋ ቀና በማለት በቁጣና በከረረ ቃል የተገለጡትን ሊቀጠበብት ዘሪሁንን ጀግናው የወንጌል አርበኛና የቅኔ ባለሞያው መሪጌታ ሙሴ መንበሩ በተረጋጋና በሰከነ አነጋገር ፈገግታን ተላብሰው የጅብ ችኩል ቀንድ ይነክሳል የሚለውን ምሳሌ በመጠቀም ሊቀጠበብት ዘሪሁን ምንም እንኳ ከተቀበሉት ማዕረግ የተነሳ ሊቀጠበብት የተሰኙ ቢሆንም ያላዋቂ ሳሚ ንፍጥ ይለቀልቃል እንደሚባለው  የሊቀጠበብት ዘሪሁን መልሳቸው  ከስማቸው ጋር ፍጹም የማይገናኝና በዚሁ  በቃለ እግዚአብሔር መልሳቸውም ገና ያልበሰሉ ብዙ መማር የሚጠበቅባቸው ልጅ መሆናቸውን አጉልቶ የሚያሳይ  በመሆኑ ለሊቀጠበት ዘሪሁን እንዲህ ሲሉ የመወድሱን ቅኔ ደረደሩላቸው ቅኔውም እንዲህ የሚል ነው ዘሪሁን ዝሂብ እንተ ለከርሱ ፍጡነ በረዊጽ አሃዘ ጽጌ ስጦታው ቀርነ ታድያ እኛም ይህን የሊቁንና የወንጌል መልዕክተኛውን ቅኔ ተመልክተን ይበል ብለነዋል የተወደዳችሁ ወገኖች ፍርድን ሁሉ ለውልድ ሰጠው ተብሎ ተነግሮለት በመጨረሻ በዓለም ፍጻሜ ሊፈርድ ቢመጣም አሁን ግን በአብ ቀኝ የተቀመጠ ለዘላለምም የሚኖር ብቸኛና እውነተኛ አማላጃችንና አስታራቂያችን ነው ትምህርቱን በዚህ ጠቅልለናል የምታነቡና በትምህርቱም ተጠቃሚ የሆናችሁ ጌታ እግዚአብሔር ይባርካችሁ ለማለት እወዳለሁ

ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን

ቀሲስ አባ ዮናስ ጌታነህ

No comments:

Post a Comment