Friday 5 December 2014

ክፍል ሦስት



ክፍል ሦስት

ወዘእንበለ ይብጻሕ አሚን ዐቀበተነ ኦሪት
ወመርሐተነ ውስተ አሚን ዘይመጽእ ኦሪት
እንከ መርሃ ኮነተነ ለኀበ ክርስቶስ ከመ ንጽ
ደቅ በአሚን ቦቱ ወሶበ መጽአት እንከ አሚን
ኢንፈቅድ እንከ መርሃ

ትርጉም፦ እምነትም ሳይመጣ ሊገለጥ ላለው እምነት ተዘግተን ከሕግ
በታች እንጠበቅ ነበር እንደዚህ በእምነት እንጸድቅ ዘንድ
ሕግ ወደ ክርስቶስ የሚያመጣ ሞግዚታችን ሆኖአል እምነት
ግን መጥቶአልና ከእንግዲህ ወዲህ ከሞግዚት በታች አይደለንም

ገላትያ 3 23 _ 25

ሕጉንም የሚጠብቁ ሰዎችን
እንደ አደራ ገንዘብ ይጠብቃቸዋል

2
መቃብያን 12 7

የአዋልድ መጻሕፍት የውስጥ ገበና ሲገለጥና በእግዚአብሔር ቃል ሲፈተሽ

መጽሐፍቅዱሳችን በገላትያ መጽሐፍ ላይ ሕግ ወደ ክርስቶስ የሚያመጣ ሞግዚታችን ነው እያለን የመቃብያን ጸሐፊ ግን ሕጉንም የሚጠብቁ ሰዎችን እንደ አደራ ገንዘብ ይጠብቃቸዋል ማለቱ ከምን ያመጣው ሃሳብ ነው ? ሕግ ሰዎችን ወደ ክርስቶስ የሚያመጣ ሞግዚት እንጂ ሕግ ተጠብቆ ሰዎችን ለእግዚአብሔር ባላደራ የሚያደርግ አይደለም እግዚአብሔር እንደ አደራ ገንዘብ የሚጠብቃቸው ሰዎች በሕግ ሞግዚትነት ወደ ክርስቶስ የመጡትንና ይህንኑ ጌታ በነፍስ ወከፍ አዳኛቸው አድርገው የተቀበሉትን ነው መጽሐፍቅዱሳችን ለተቀበሉት ሁሉ ግን በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው ይለናልና የዮሐንስ ወንጌል 1 12 የእግዚአብሔር የአደራ ገንዘብ የሚባሉት እግዚአብሔር በልጁ ደም የገዛቸው ልጆቹ ናቸው እንጂ ሕጉን የጠበቁ አይደሉም 1 ጴጥሮስ 1 19 _ 21 ለዚህ ነው መጽሐፍቅዱሳችን ወኢኮንክሙ ለርእስክሙ በሤጥ ተሣየጠክሙ ሰብሕዎ ለእግዚአብሔር በሥጋክሙ የሚለን ትርጉም በዋጋ ተገዝታችኋልና ለራሳችሁ አይደላችሁም ስለዚህ በሥጋችሁ እግዚአብሔርን አክብሩ 1 ቆሮንቶስ 6 19 እና 20 ስለዚህ በዋጋ የገዛን ደሙ እንጂ ሕጉ አይደለም ሕጉማ እኛን ወደ ክርስቶስ ሊያመጣን ከሞግዚትነት አላለፈም እግዚአብሔርም እንደ አደራ ገንዘቡ የሚጠብቀን የልጁ ደም ስለ ፈሰሰልንና ልጆቹ ስለሆንን እንጂ ሕጉን ስለጠበቅን አይደለም ከዚህም የተነሳ አሁን ከሞግዚት በታች አይደላችሁም ተብለናል ነገር ግን የፈሰሰላቸውን ደም አይተውና ጌታን መቀበል ትተው ወደ ሕግ የተመለሱትን ሕጉንም የሚጠብቁ ሰዎች ውሳኔያቸውን አስተካክለው ወደ ጌታ ካለመምጣት የተነሳ እስከ አሁን ድረስ በሕግ ሞግዚትነት ሥር ይኖራሉ ይህ እንግዲህ በጣም የሚያሳዝን ነገር ነው እንግዲህ እስከ መቼ በሞግዚት ሥር እንደሚቀጥሉ ባናውቅም በደሙ ተዋጅተው እግዚአብሔር በአደራነት የሚጠብቃቸው ልጆቹ እንዲሆኑ እንጸልይላቸዋለን ሕግ ሞግዚት ብቻ ሳይሆን እምነት እስኪመጣ ድረስ ሊመጣ ላለው እምነት ዘግቶን በበታች ያስቀመጠን ነበር አሁን ግን በክርስቶስ የሆነው እምነት ስለመጣልን የሕጉ የበታች አይደለንም የሚያምኑ ሁሉ ይጸድቁ ዘንድ ክርስቶስ የሕግ ፍጻሜ ነውና ሮሜ 10 4 ስለዚህ ለጽድቃችን ክርስቶስ ከፈጸመልን ሕግ የተነሳ ሕጉ የበታች አድርጎ ዘግቶ ሊያስቀምጠን አልቻለም ታድያ ክርስቶስ በፈጸመው ሕግ አምነው የጸደቁ ሕጉ የበታች አድርጎ ዘግቶ ካስቀመጣቸው ውስጥ ሲያመልጡ ያላመኑ ግን በዚያው ሕጉ ባስቀመጣቸው የበታቹ ሥፍራ ተዘግተው ይኖራሉ ሕጉ አልዘጋባቸውም እንደውም ያላቸው እምነት መጥቷል ስለዚህ ለተገለጠው እምነት የዘጋሁትን በር ከፍቼ ወደ ክርስቶስ ላደርሳቸው ሞግዚት ሆኛቸዋለሁ ፈቃዳቸው ከሆነ ወደ ክርስቶስ አደርሳቸዋለሁ ካልፈቀዱ ግን ምርጫው የእነርሱ ነው እያለ ነው እንግዲህ ምርጫን ማስተካከል የራስ ጉዳይ ነው በመሆኑም ታድያ ወደ ክርስቶስ የሚያደርስ ሞግዚት እያለ አልፈልግም ሲሉ በሞግዚት ሥር መቀመጥ በሕግ የበታችነትም ተዘግቶ መኖር አላዋቂነት ነው አንዳንዶች ደግሞ እንጠብቀዋለን የሚሉትን ሕግ እንኳ በቅጡ ሳያውቁ በእንቶ ፈንቶው በአሻሮውና በባለ ሳምንት ጽዋው ተጀቡነው ተከናንበውና ተዘግተው ይኖራሉ ይሄ ደግሞ ትልቁና አስከፊው ሃይማኖታዊ በሽታ ነው እግዚአብሔር ከዚህም እንዲፈውስ ጸሎታችን ነው እንግዲህ ይህንን ሁሉ ሊያስጥል የሚችል በክርስቶስ ኢየሱስ የሆነው እምነታችን ነውና ክርስቶስን ስናምን የኃጢአትን ይቅርታ እንቀበላለን እርሱን ስናምን የዘላለምን ሕይወት እናገኛለን እግዚአብሔር ለዚህ ይርዳን

ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን

ቀሲስ አባ ዮናስ ጌታነህ

No comments:

Post a Comment