Friday 5 December 2014

ክፍል አራት




ክፍል አራት

እስመ ኮነ ተዋልጦ በቀዳሚ ሕግ በእንተ ድካም እስመ አልባቲ
ባቁዕ ወኢያስለጠት ወኢምንተኒ ኦሪት ወባሕቱ ቦአ ተስፋ ሕየንቴሃ
ዘይሄይስ እምኔሃ ወቦቱ ንቀርቦ ለእግዚአብሔር

ትርጉም፦ ሕጉ ምንም ፍጹም አላደረገምና ስለዚህም የምትደክም
የማትጠቅምም ስለሆነች የቀደመች ትእዛዝ ተሽራለች
ወደ እግዚአብሔርም የምንቀርብበት የሚሻል ተስፋ ገብቶአል

ዕብራውያን 7 18 እና 19

ሕጉንም የሚጠብቁ ሰዎችን
እንደ አደራ ገንዘብ ይጠብቃቸዋል

2
መቃብያን 12 7

በክፍል አራት ትምህርታችን ላይ ሕጉን አስመልክቶ ብዙዎች የምትደክም የማትጠቅም ስለሆነች የቀደመች ትዕዛዝ ተሽራለች የሚለውን ሃሳብ ይዘው የሚሻል ተስፋ ኢየሱስ ስለመጣ ሕጉ ተሽሮአልና ዋጋ የለውም ልንጠብቀውም አያስፈልግም ብለው ያስባሉ ጌታ ደግሞ ሕግንና ነቢያትን ሊሽር እንዳልመጣ በትምህርቱ ተናገረን ኢይምሰልክሙ ዘመጻእኩ እስዓሮሙ ለኦሪት ወለነቢያት ዘእንበለ ዳዕሙ ከመ እፈጽሞሙ አማን እብለክሙ እስከ አመ የኀልፍ ሰማይ ወምድር የውጣ እንተ አሐቲ ኅርመታ ወአሐቲ ቅርፀታ ኢተኀልፍ እምኦሪት ወእምነቢያት እስከ ሶበ ኩሉ ይትገበር ወይከውን ትርጉም እኔ ግን ሕግንና ነቢያትን ለመሻር የመጣሁ አይምሰላችሁ ልፈጽም እንጂ ለመሻር አልመጣሁም እውነት እላችኋለሁ ሰማይና ምድር እስኪያልፍ ድረስ ከሕግ አንዲት የውጣ ወይም አንዲት ነጥብ ከቶ አታልፍም ሁሉ እስኪፈጸም ድረስ አለ የማቴዎስ ወንጌል 5 17 _ 19 ከዚህም ሌላ ሕጉ ቅዱስ ነው ትዕዛዚቱም ቅድስትና ጻድቅት በጎም ናት ይለናል ሮሜ 7 12 እንግዲህ ኢየሱስ ሕግን ሊፈጽም እንጂ ሊሽር የመጣ ካልሆነ እንደገናም ከሕግ አንዲት የውጣ ወይም ነጥብ የማታልፍ ከሆነ ሕጉም ቅዱስ ጻድቅና በጎ ከተባለ የዕብራውያን ጸሐፊ ስለ ሕጉ በማውሳት የምትደክም የማትጠቅም ስለሆነች የቀደመች ትዕዛዝ ተሽራለች ሲል ምን ለማለት የፈለገ ይመስላል ? የሚል ጥያቄ ማስነሳቱ አይቀርም ይህንን በአጭሩ ለመመለስ ሕጉ ሲሰጥ ለሕይወት የተሰጠ ሕግ መሆኑን ይናገራል ሮሜ 7 10 በተጨማሪም ሙሴ ስለተቀበለው የሕይወት ቃል ሲናገር ይሰጠንም ዘንድ ሕይወት ያላቸውን ቃላት ተቀበለ ይለናል የሐዋርያት ሥራ 10 38 ስለዚህ እግዚአብሔር ሕጉን ሲሰጥ የሰጠበት ምክንያት ለሕይወት ነው እንጂ ለሞት አይደለም ነገር ግን የሰው ልጅ ይህንን ለሕይወት የተሰጠውን ሕግ በማንነቱ መጠበቅ ስላልቻለ ለሞት ሆነበት ለዚህም ነው ሐዋርያው ኃጢአት ምክንያት አግኝቶ በትእዛዝ አታሎኛልና በእርስዋም ገድሎኛል ሲል የተናገረው ሮሜ 7 7 _ 12 ሕጉ ቅዱስ ጻድቅና በጎ ብቻ ሳይሆን ሕጉ መንፈሳዊ ነው ሕጉ መልካም ነው ሮሜ 7 14 17 ጳውሎስ ገደለኝ የሚለው ኃጢአትን ነው እንጂ ሕጉን ወይም ትዕዛዙን አይደለም ሕጉማ ሊለወጥ ሊሻሻል ሊበረዝ ሊከለስ የማይችል ሕግ ነው ትዕዛዙም እንዲሁ ትዕዛዝ ነው ኃጢአት ያለ ሕግ ምውት ነበር ትዕዛዝ በመጣ ጊዜ ግን ኃጢአት ሕያው ሆነ ለዚህ ነው ጳውሎስ በሕግ ባይሆን ኃጢአትን ባላወቅሁም ነበር ሕጉ አትመኝ ባላለ ምኞትን ባላወቅሁም ነበር ሲል የተናገረው ስለዚህ ሕግ ሳያደላ ወይም በዘመኑ አነጋገር ሳያመቻምች ትክክለኛውን ነገር የሚናገር በመሆኑ ትዕዛዝ በመጣች ጊዜ ግን ኃጢአት ሕያው ሆነ እኔም ሞትኩ በማለት ሲናገር እንመለከታለን ሞት የሚያስጨንቅ ነገር በመሆኑ አያይዞም እኔ ምንኛ ጐስቋላ ሰው ነኝ ? ለዚህ ሞት ከተሰጠ ሰውነት ማን ያድነኛል ? የሚል ጥያቄ ያነሳል ይህ ጥያቄ እንግዲህ የጳውሎስ ብቻ ሳይሆን የሁላችንም ጥያቄ ነው አሁንም ለዚህ ለሞት ከተሰጠ ሰውነት ማን ያድነናል ? መልሱ አንድና አንድ ነው ኃጢአት ያመጣብን ሞት አለ ከዚህ ሞት ሊያድነን የሚችል ብቸኛ መድኃኒት የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው እንዴት ነው ያዳነን ስንል በኃጢአት ምክንያት የመጣብንን ሞት ሞቶልን አዳነን ሮሜ 4 22 _ 25 1 ጴጥሮስ 2 24 እስከ 25 እንደገናም እኛ በሥጋ ልንፈጽመው ያልቻልነውን ሕግ እርሱ ፈጽሞ አዳነን ሮሜ 10 4 ነገር ግን የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት የተወለደውን ከሕግም በታች የተወለደውን ልጁን ላከ እንደ ልጆች እንሆን ዘንድ ከሕግ በታች ያሉትን ይዋጅ ዘንድ ይለናል ገላትያ 4 4 ኢየሱስ እንደ ልጆች ሊያደርገን ከሕግ በታች ተወልዶ ነው ልንጸድቅበት ያልቻልነውን ሕግ የፈጸመልን ታድያ ይሄ ሕግ ጠብቀነው ሊያጸድቀን ያልቻለ ብቻ ሳይሆን በእርግማን በታች ሳይቀር የሆንበት ሕግ ነው ኢየሱስ ግን ስለ እኛ እርግማን ሆኖ ከዚህም የሕግ እርግማን ዋጀን ገላትያ 4 10 _ 14 እንግዲህ አሁን ሕግን የምንፈጽምበት መንገዱ የመቃብያን ጸሐፊ እንደተናገረው ሕጉን ጠብቀን እግዚአብሔር እንደ አደራ ገንዘቡ ያየናል በሚል መንፈስና ሃሳብ ሳይሆን በሮሜ 8 3 _ 5 ከሥጋ የተነሳ ስለ ደከመ ለሕግ ያልተቻለውን እግዚአብሔር የገዛ ልጁን በኃጢአተኛ ሥጋ ምሳሌ በኃጢአትም ምክንያት ልኮ አድርጎአልና እንደ መንፈስ ፈቃድ እንጂ እንደ ሥጋ ፈቃድ በማንመላለስ በእኛ የሕግ ትዕዛዝ ይፈጸም ዘንድ ኃጢአትን በሥጋ ኮነነ ይለናል ስለዚህ የሕግ ትዕዛዝ የሚፈጸመው እንደ መንፈስ ፈቃድ ስንመላለስ ነው የሕጉን ትእዛዝ ለመፈጸምና እንደ መንፈስ ፈቃድ ለመመላለስ ደግሞ ይህንን ሁሉ ዋጋ ከፍሎ የተቤዠንን ጌታ አምኖ መቀበል ዋናውና አስፈላጊው ነገር ነው እንደውም በሮሜ 8 1 ላይ እንግዲህ በክርስቶስ ኢየሱስ ላሉት አሁን ኩነኔ የለባቸውም በክርስቶስ ኢየሱስ ያለው የሕይወት መንፈስ ሕግ ከኃጢአትና ከሞት ሕግ አርነት አውጥቶኛልና ይለናል በመሆኑም አሁን ያለው ሕግ ክርስቶስ ኢየሱስ የፈጸመው በመሆኑ በክርስቶስ ኢየሱስ ያለው የሕይወት መንፈስ ሕግ ነው ታድያ ከሥጋ የተነሳ ስለደከመ ለሕግ ያልተቻለውን እያለን እኛ ግን ከመቃብያን ሃሳብ አንወጣም በማለት እንዲሁ በሥጋ ተነስተን ሕግን ፈጽመን የእግዚአብሔር ባለ አደራ ገንዘብ እንሆናለን ማለት ፍጹም መሳሳት ይሆንብናልና አይሆንም እንደገናም ሕጉ ምንም ፍጹም አላደረገምና ስለዚህ የምትደክም የማትጠቅም ነች የተባለው እኛ ጠብቀነው ልንጸድቅበት ካለመቻላችን የተነሳ እንጂ ሕጉ ደካማና የማይጠቅም ሆኖ አይደለም እንግዲህ የዕብራውያን ጸሐፊ በማያዳግም ሁኔታ ወደ እግዚአብሔር የምንቀርብበት የሚሻል ተስፋ ገብቶአል እያለን ነው እርሱን በሚቀጥለው ክፍለ ጊዜያችን በስፋት የምንመለከተው ይሆናል እስከዚያው ሰላምና ጸጋ ከእናንተ ጋር ይሁን የምላችሁ

ወንድማሁ ቀሲስ አባ ዮናስ ነኝ

ጌታ ይባርካችሁ



No comments:

Post a Comment