Sunday 7 December 2014

የማርያምን ትንሣኤ እንደ ልጇ ትንሣኤ……………

የመልዕክት ርዕስ …………………. ትንሣኤሃ ለማርያም ከመ ትንሣኤ ወልዳ


የማርያምን ትንሣኤ እንደ ልጇ ትንሣኤ……………


የማርያምን ትንሣኤ እንደ ልጇ ትንሣኤ

አድርጋችሁ አክብሩ

አኮኑ በእንቲአነሂ እለ አመነ በዘአንሥኦ ለእግዚእነ እምውታን 
ዘተሰቅለ በእንተ ኃጢአትነ ወተንሥአ ከመ ያጽድቀነ ወከመ ያንሥአነ

ኀበ ሰብአ ሮሜ ምዕራፍ 4 ፥ 24 እና 25

ትርጉም፦ ስለ በደላችን አልፎ የተሰጠውን እኛን ስለማጽደቅም የተነሣውን
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ከሙታን ባስነሣው ለምናምን ለእኛ
ይቆጠርልን ዘንድ አለው

ወደ ሮሜ ሰዎች ምዕራፍ 4 ፥ 24 እና 25 

ክፍል ሦስት


 




በዚህ በክፍል ሦስት ትምሕርታችን ላይ የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ሞትና ትንሣኤ ምስጢር ምን እንደሆነ የሚያስተምረንን ነገር በስፋት እንመለከታለን አብዛኛው ሰው ኢየሱስ እንደሞተና እንደተነሳ ያውቃል ይተርካል ይናገራል ነገር ግን የሞተበትና የተነሳበትን ምክንያት በውል ያልተረዳው ስለሆነ ለእኛ ነው የሞተው ለእኛ ነው የተነሳው ብሎ ቢናገርም ይህንን በዘልማድ ከሚናገር ውጪ በእምነት ለእኔ ነው ብሎ ስላልወሰደው ከበደሌ ነጽቻለሁ ጸድቄያለሁ ለማለት አቅም ያጣል ጸድቀሃል ወይ ሲሉትም እርሱንማ እላይ ስሄድ ነው የማውቀው ይላል እዚህ በምድር ላይ ሳለን የኢየሱስን ሞትና ትንሣኤ በማመናችን ምክንያት መጽደቃችንን ካላወቅን በሰማይም አናውቅም እንደውም መጽደቃችንን በዚሁ በምድር ላይ በስጋ ሕይወታችን አምነን ካልተቀበልን በሰማይ የሚጠብቀን የገሃነም ፍርድ ነው ስለዚህ መጽደቃችንንም ሆነ መዳናችንን እዚሁ በምድር ላይ ሳለን ለማረጋገጥ ዛሬ ነገ ሳንል አሁኑኑ ወደ ኢየሱስ እንምጣ ኢየሱስንም የሕይወታችን ጌታና አዳኝ አድርገን እንቀበል የመዳን ቀን አሁን ነውና መጽሐፍቅዱሳችን በተወደደ ሰዓት ሰማሁህ በመዳንም ቀን ረዳሁህ ይላልና እነሆ የተወደደው ሰዓት አሁን ነው እነሆ የመዳን ቀን አሁን ነው ይለናል 2ኛ ቆሮንቶስ 6፥2 እንደገናም ለተቀበሉት ሁሉ ግን በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው ስለሚለን የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስን በመቀበልና ወደ ሕይወታችን በማስገባት የእግዚአብሔር ልጆች እንሆናለን የዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ 1 ፥ 12 ከዚያ ውጪ ግን ልጅነት የለም ኢየሱስን በመቀበል ከእግዚአብሔር ያልተወለደ ልጅ አይባልም ልጅ ካልሆነ ደግሞ አይወርስም ምክንያቱም መጽሐፍቅዱስ ልጆች ከሆንን ወራሾች ደግሞ ነን ማለት የእግዚአብሔር ወራሾች ነን ይለናል ሮሜ 8 ፥ 17 ታድያ የእግዚአብሔር ወራሽ መሆን ምንኛ መታደል ነው ? እግዚአብሔር እንደ ሰው ጠፊ አላቂ የሆነውን የዚህ ዓለም ነገር አይደለም የሚያወርሰን መንግሥቱንና ጽድቁን እስከፈለግን ድረስ ይህንንም ሊሰጠን የታመነ ነው የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 6 ፥ 33 እግዚአብሔር የሚያወርሰን መንግሥተ ሰማያትን ነው ኢየሱስን አምኖ የተቀበለ ሁሉ የመንግሥተ ሰማያት ወራሽ ነው የመንግሥተ ሰማያት ወራሽ ለመሆን ግን በኢየሱስ አምኖ የጸደቀ ጻድቅ ወይም ጻድቃን መሆን ያስፈልጋል የተራበ ለማብላት የተጠማ ለማጠጣትና የመሳሰሉትን ለማድረግ በመጀመርያ ጻድቅ ወይም ጻድቃን መሆን ዋነኛ ነገር ነው በኢየሱስ አምነን ጻድቅ ሳንሆን ብናበላ ብናጠጣና ሌሎችንም በጎ የሆኑ ነገሮችን ብናደርግ ለጽድቃችን የሚቆጠር ነገር ስለሌለ ዋጋ የለውም እግዚአብሔር ለጽድቃችን የቆጠረው ያበላነውን ያጠጣነውን በጎ ያደረግናቸውን ነገሮች ሁሉ ሳይሆን ኢየሱስን ነው መጽሐፍ ሲናገር እንዲህ አለ እስመ ዘኢየአምር ኃጢአተ ረሰዮ ኃጥእ በእንቲአነ ከመ ኪያነ ያጽድቀነ ለእግዚአብሔር ትርጉም እኛ በእርሱ ሆነን የእግዚአብሔር ጽድቅ እንሆን ዘንድ ኃጢአት ያላወቀውን እርሱን ኃጢአት አደረገው 2ኛ ቆሮንቶስ 5 ፥ 21 ለዚህ ነው ኢየሱስ በተራ በረድፍ ላቀረባቸው ዝርዝር ሃሳቦች ጻድቃንም መልሰው ይሉታል ጌታ ሆይ ተርበህ አይተን መቼ አበላንህስ ? ወይስ ተጠምተህ አይተን መቼ አጠጣንህ ? እና የመሣሠሉትን ነገሮች ሁሉ የተናገሩት የማቴዎስ ወንጌል 25 ፥ 31_46 ማብላት ማጠጣት እንግዳ መቀበል እና ሌሎችም መልካም ምግባራት አስፈላጊዎች ቢሆኑም ኢየሱስን እንደ ግል አዳኝ አድርጎ ከመቀበልና ከመጽደቅ መልስ የሚደረጉ ነገሮች ናቸው በመጀመርያ ግን ኢየሱስ የሕይወታችን ጌታ ሊሆን ይገባል እንደገናም አጽዳቂው ኢየሱስ ስለሆነ ለጽድቃችን የጠየቀን ነገር የለም 1ኛ ቆሮንቶስ 6 ፥9_11 ለጽድቃችን ደግሞ የሠራነው ሥራ አለ ፣ እንዲህና እንዲያ አደረግን ፣ እናደርጋለን ብለን ብናስብ እንኳ ጽድቃችን የመርገም ጨርቅ ነው ኢሳይያስ 64 ፥ 6 ከፈሪሳዊው ይልቅ ቀራጩ ጻድቅ ሆኖ የተመለሰው ፈሪሳዊው ጽድቁን ሲቆጥር ነው ቀራጩ ግን የሚቆጥረው ጽድቅ አልነበረውም እንዲሁ ከሩቅ ሆኖ እኔን ኃጢአተኛውን ማረኝ እያለ ደረቱን ይደቃ ነበርና ጻድቅ ሆኖ ተመለሰ ይለናል የሉቃስ ወንጌል 18 ፥ 9_15 ለዚህ ነው መጽሐፍ ቅዱሳችን ወዘሰ ተቀንየ ኢይከውኖ ዐስበ ከመ ዘጸገውዎ አላ ከመ ዘይደልዎ ወዘሰ ኢተቀነየ ለእመ ተአመነ በዘያጸድቆ ለኃጥእ ይትኌለቆ ጽድቀ አሚኖቱ የሚለን ትርጉም ለሚሠራ ደመወዝ እንደ ዕዳ ነው እንጂ እንደ ጸጋ አይቆጠርለትም ነገር ግን ለማይሠራ ኃጢአተኛውን በሚያጸድቅ ለሚያምን ሰው እምነቱ ጽድቅ ሆኖ ይቆጠርለታል አለን ሮሜ 4 ፥ 4 እና 5 ስለዚህ የእኛ ሥራ ሳይጨመርበት ኢየሱስ ክርስቶስ በሠራልን ሥራ ብቻ ወደ አብ መንግሥት እንገባለን ኤፌሶን 2 ፥ 18 የእግዚአብሔር ልጅ ጌታ ኢየሱስ መጸነሱ መወለዱ መሞት መነሳቱ ትርጉም አለው ትርጉሙም እኛን የማዳን ትርጉም ነው ወእመሰኬ ክርስቶስ ኢተንሥአ እምውታን ከንቱ ውእቱ ትምህርትነ ወከንቶ ተአመንክሙ ቦቱ ወንሕነኒ ኮነ ሰማዕተ ሐሰት ላዕለ እግዚአብሔር እስመ ንቤ አንሥኦ ለክርስቶስ ዘኢያንሥኦኑ እንከ ትርጉም ክርስቶስም ካልተነሣ እንግዲያስ ስብከታችን ከንቱ ነው እምነታችሁም ደግሞ ከንቱ ናት ደግሞም ክርስቶስን አስነስቶታል ብለን በእግዚአብሔር ላይ ስለ መሰከርን ሐሰተኞች የእግዚአብሔር ምስክሮች ሆነን ተገኝተናል ይለናል 1ኛ ቆሮንቶስ 15 ፥ 14 እና 15 ብዙዎች ጻድቃን ቅዱሳን ማርያምንም ጨምረን ሞቱ ብንላቸው የሞቱት ለራሳቸው ነው ኢየሱስ ግን ለእኔና ለእናንተ ኃጢአት ነው የሞተው መጽሐፍ ቅዱሳችን በዚህ ጉዳይ ላይ አሁንም ስለ ጻድቅ የሚሞት በጭንቅ ይገኛልና ስለ ቸር ሰው ግን ሊሞት እንኳ የሚደፍር ምንአልባት ይገኝ ይሆናል ነገር ግን ገና ኃጢአተኞች ሳለን ክርስቶስ ስለ እኛ ሞቶአልና እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን የራሱን ፍቅር ያስረዳል ይለናል ሮሜ 5 ፥ 7 እና 8 ጻድቅ ሆኖ ሳለ ለኃጢአተኞች የሞተ ኢየሱስ ብቻ ነው ነቢዩ ኢሳይያስ በይበልጥ ጎላ አድርጎ እርሱ ግን ስለ መተላለፋችን ቆሰለ ስለ በደላችንም ደቀቀ የደኅንነታችንም ተግሣጽ በእርሱ ላይ ነበረ በእርሱም ቁስል እኛ ተፈወስን ይለናል ኢሳይያስ ምዕራፍ 53 ን በሙሉ እናንብብ ስለበደላችን የቆሰለ የደቀቀ ከኢየሱስ ሌላ ማን ሊገኝ ይችላል ደዌያችንንና ሕማማችንን ተቀብሎ ሳለ እኛ ግን እንደ ተመታ በእግዚአብሔርም እንደ ተቀሠፈ እንደ ተችገረም ቆጠርነው የኢየሱስን መሞት ላልተረዱ ሰዎች አሁንም ያለው እውነታ ይሄ ነው በኢየሱስ አምነው መጽደቃቸውን እስካላረጋገጡ ድረስ ኢየሱስ ዛሬም ለእነርሱ በእግዚአብሔር እንደተቀሰፈ እንደተቸገረ ነው ስለዚህ እግዚአብሔር ይህንን እውነት ለብዙዎች ያብራ እያልን እንጸልያለን እግዚአብሔር ደግሞ ታማኝ ስለሆነ እውነቱን ለሕዝባችን ያበራል ወስብሐት ለእግዚአብሔር አነሳስቶ ላስጀመረን አስጀምሮ ላስፈጸመን ለልዑል እግዚአብሔር ምሥጋና ይድረሰው አሜን

ግነዩ ለእግዚአብሔር ወጸውኦ ስሞ ወንግርዎሙ 
ለአሕዛብ ምግባሮ

መዝሙረ ዳዊት 105 ፥ 1 እና 2

ቀሲስ አባ ዮናስ ጌታነህ

No comments:

Post a Comment