Thursday 10 August 2017

Ethiopian Orthodox Mezmur - Tewahedo Haymanote - Tigist Sileshi ሊታረሙ ሊስተካከሉና ሊቃኑ የሚገቡ ግጥሞችና መዝሙሮች ተዋሕዶ አንዲት እናት አባቶች የሞቱላት ተዋሕዶ እናቴ የዘላለም ቤቴ ተዋሕዶ መሠረቴ ተዋሕዶ የደም ቤቴ የዘላለም መሠረቴ …………………… ከመዝሙሮቹ መሃል ደግሞ ተዋሕዶ ሃይማኖቴ የጥንት ነሽ የእናትና የአባቴ ማኅተሜን አልበጥስም ትኖራለች ለዘላለም የግብጽን ከተሞች በደም ገንብተናል በመንገድ ጽድቅ የለም ሞተን ግን ኖረናል ማኅተምሽን ፍቺ በጥሺው ቢሉኝ እኔስ ከነ አንጌቴ ውሰዱት አልኩኝ ጴጥሮስ ተሰቀለ ጳውሎስ ተሰየፈ ተዋሕዶ እያለ አረ ስንቱ አለፈ ………………………. በማለት ዘምረዋል የኢየሱስ አማላጅነት ( ክፍል አስር ) ከሚለው ትምህርት ጋር ተያይዞ የቀረበ የተወደዳችሁ የእግዚአብሔር ሕዝቦች ሰላም ለእናንተ ይሁን በክፍል አስር ትምህርታችን የኢየሱስን አርአያነትና ምሳሌነት አስመልክቶ ኢየሱስ የመታዘዝ ምሳሌ መሆኑን ያየንበት ክፍል ነው ኢየሱስ ለአባቱ የታዘዘው የአባቱን ቃል ስለሰማ ነው ታድያ ይሄ መታዘዙ ለመስቀል ሞት ሳይቀር ወደመታዘዝ ወሰደው ከዚህም የተነሳ በዮሐንስ ወንጌል 19 ፥ 30 ላይ እንደምንመለከተው ኢየሱስም ሆምጣጤውን ከተቀበለ በኋላ ተፈጸመ አለ ራሱንም አዘንብሎ ነፍሱን አሳልፎ ሰጠ ታድያ ይህ ነፍስን አሳልፎ የመስጠት ሕይወት ነው የዘላለምን መዳን ያመጣልን በዚህ ነፍስን አሳልፎ የመስጠት ሕይወት ውስጥ ዓለቶች ተሰነጠቁ ፣ የጥል መጋረጃ ተቀደደ ፣ ሰውና እግዚአብሔር ታረቀ ፣ ዳግመኛም ከእግዚአብሔር መወለድ ተገኘ ፣ ይህንን የመሣሠሉ የደኅንነት ሥራዎች በኢየሱስ ሞትና ትንሣኤ ተከናወኑ ይህ ነፍስን አሳልፎ የመስጠት ሕይወት የተጠናቀቀው በመስቀል ሞት በመሆኑ ከዚህ የመስቀል ሞት መልስ ኢየሱስን እግዚአብሔር ያለ ልክ ከፍ ከፍ አደረገው ከስሞች ሁሉ በላይ ያለውን ስም ሰጠው ይህም በሰማይና በምድር ከምድርም በታች ያለ ፍጥረት ሁሉ ለኢየሱስ ይንበረከክ ዘንድ ምላስም ለእግዚአብሔር አብ ክብር ይሰጥ ዘንድ ኢየሱስ ጌታ እንደሆነ ይመሰክር ዘንድ ነው ፊልጵስዩስ 2 ፥ 5 _ 11 በመሆኑም ይሄ እውነት ለአባቶች የተሰጠ ተስፋ የምሥራች በመሆኑ ሐዋርያቱ ይህንን የምሥራቹን ለእናንተ እንሰብካለን ካሉን በኋላ ሃሳቡን አጠናክረውት ደግሞ እንዲህ አሉን ይህን ተስፋ እግዚአብሔር በሁለተኛው መዝሙር ደግሞ አንተ ልጄ ነህ እኔ ዛሬ ወለድሁህ ተብሎ እንደተጻፈ ኢየሱስን አስነስቶ ለእኛ ለልጆቻቸው ፈጽሞአልና በማለት በኢየሱስ አማካኝነት በተፈጸመ የደኅንነት ሥራ ውስጥ ዛሬ ላይ የምንገኝ መሆኑን አስረግጠው ነገሩን ( የሐዋርያት ሥራ 13 ፥ 30 _ 34 ) ስለዚህ አሁን የአባቶች ተስፋ የምሥራች የሆነውን ኢየሱስን አስነስቶ ለእኛና ለልጆቻቸው ጌታ እግዚአብሔር የመዳናችንን ተስፋ ፈጽሞታል እውነቱ ይሄ ነው ወገኖቼ ስለዚህ አሁን ከእኔና ከእናንተ ከሰው ልጆች ሁሉ የሚጠበቀው በሮሜ 10 ፥ 14 _ 17 መሠረት ለተገለጠውና አባቶችም ተስፋ አድርገውት እኛን ስለማጽደቅ ከሞት በመነሣት ለተጠናቀቀው ለምሥራቹ ቃል መታዘዝ ነው ይሁን እንጂ ይኸው የክፍሉ ሃሳብ እንደነገረን ነገር ግን ሁሉ ለምሥራቹ ቃል አልታዘዙም ይለናል ስለዚህ ሃይማኖት ማለት በእግዚአብሔር ቃል የሆነ መስማትን አግኝቶ እና አምኖ ለምስራቹም ቃል ታዞ መዳን ነው በመሆኑም ሃይማኖት በእግዚአብሔር ቃል እምነት የሚመጣ እንጂ የእናትና የአባቴ የሚባልና ሲባልም የሚዘመር አይደለም በዚህ በትምህርቴ ላይ አንድ ሃሳብ አንስቼ ነበር ሰዎች እውነተኛውን ወንጌል ለመቃወም ሲሉና እምነታቸውንም ያስጠበቁ እየመሰላቸው ያሉትን ነገር በመጠኑም ቢሆን ጠቁሜ ነበር አሁንም ዘርዘር አድርጌ ሃሳቡን አነሳዋለሁ በግጥምም ስንኝ ይሁን በነጠላ የዜማ ግጥማቸው እንዲህ ሲሉ አንዳንድ ሰዎች ተናግረዋል ፣ ገጥመዋል ፣ አዚመዋል በመሆኑም ከግጥሞቹ መሃል ጥቂቱንና ከዜማዎቹም መካከል የተወሰኑትን እናያለን በመጀመርያ ግጥሞቹ እንዲህ የሚሉ ናቸው ተዋሕዶ አንዲት እናት አባቶች የሞቱላት ተዋሕዶ እናቴ የዘላለም ቤቴ ተዋሕዶ መሠረቴ ተዋሕዶ የደም ቤቴ የዘላለም መሠረቴ …………………… ከመዝሙሮቹ መሃል ደግሞ ተዋሕዶ ሃይማኖቴ የጥንት ነሽ የእናትና የአባቴ ማኅተሜን አልበጥስም ትኖራለች ለዘላለም የግብጽን ከተሞች በደም ገንብተናል በመንገድ ጽድቅ የለም ሞተን ግን ኖረናል ማኅተምሽን ፍቺ በጥሺው ቢሉኝ እኔስ ከነ አንጌቴ ውሰዱት አልኩኝ ጴጥሮስ ተሰቀለ ጳውሎስ ተሰየፈ ተዋሕዶ እያለ አረ ስንቱ አለፈ ………………………. በማለት ዘምረዋል ታድያ አባቶች የሞቱት በእግዚአብሔር ቃል እምነት ውስጥ ላለና ኢየሱስን በማስነሳት መዳን ለተፈጸመበት የምሥራቹ ቃል ነው ? ወይስ ገጣሚው እንደነገረን አንዲት ለተባለች የተዋሕዶ እምነት ? ተዋሕዶን ተዋሕዶ እምነት የሚያሰኘው ይሄ የዘረዘርኩት እውነት በዚህ ሃይማኖት ውስጥ ሲኖርና ሲገኝ ብቻ ነው ታድያ አባቶች በዚህ ሃይማኖት ውስጥ ላለ ለተገለጠው ለእግዚአብሔር ቃል እውነት ኖረውና ሞተው ከሆነ እሰየው አለበለዚያ ግን ይሄ ካልሆነ ግጥሙም ሆነ ዜማው የባዶ ሜዳ ሽለላና ቀረርቶ ነው ሲመስለኝ ግን ገጣሚውም ሆነ ዘማሪዋ ከእግዚአብሔር ቃል ተነስተው ሳይሆን ይህንን ያሉት ከተዋሕዶ ሃይማኖታዊ ቅንዓት ተነስተው ስለሆነ ግጥሙም ሆነ ዜማው የእግዚአብሔርን ቃል መሠረት ያላደረገ በመሆኑ ፉርሽ ነው ቤትና ባለጠግነት ከአባቶች ዘንድ ይወረሳሉ፤ አስተዋይ ሚስት ግን ከእግዚአብሔር ዘንድ ናት እንደሚል ቃሉ ምሳሌ 19 ፥ 14 ከአባቶች የሚወረስ ቤትና ባለጠግነት እንጂ ሃይማኖት ከአባቶች አይወረስም ይሁን እንጂ ቃሉን ለእኛ አስተላልፈውልን ትክክለኛ የሆነው ቃሉ ካለን ግን ይቻላል ዕብራውያን 2 ፥ 3 እና 4 ፤ የሉቃስ ወንጌል 1 ፥ 1 _ 4 ደግሞም በመሠረቱ ሰው መሞት ካለበት መሞት ያለበት ለሃይማኖት አይደለም ለተገለጠው የእግዚአብሔር ቃል እውነት ነው መሞት ያለበት አባቶችም የሞቱት በሃይማኖት ውስጥ ላለ ለተገለጠው ለዚሁ ለእግዚአብሔር ቃል እንጂ ተዋሕዶ ሃይማኖቴ ፣ መሠረቴ የዘላለም ቤቴ እያለ የሞተ የትኛውም መንፈሳዊ አባት ይሁን የወንጌል አርበኛ የለም አባቶች የተሰየፉትም ሆነ የሞቱት በእግዚአብሔር ቃል እምነት መሠረት ነው እንደገናም ልዩ ልዩ የሃይማኖት ድርጅቶችና ተቋሞች ለሰዎች መሠረት ሊሆኑ አይችሉም የሰዎች መሠረት የተገለጠው የእግዚአብሔር ቃል ነው የዘላለም ቤት ያገኘነው በክርስቶስ ደም ነው እንጂ በተዋሕዶ የደም ቤቴ ባልነው ፣ በገጠምነውና በዘመርነው አይደለም ሃይማኖት በእግዚአብሔር ቃል የመጣ እምነትና በተፈጸመው የኢየሱስ መነሣት ምክንያት የአባቶች ተስፋ የሆነውን የምሥራች አምነን ሰምተንም የምንድንበት እንጂ የጥንትነሽ የእናትና አባቴ ስንል የምናውጀውም ሆነ የምንዘምረው አይደለም ጌታ የሰጠን ማኅተም ደግሞ የበጉ ደም ነው እንጂ እኛ አንበጥስም ትኖራለች ለዘላለም ስንል ያዘጋጀነው ጥቁር ወይንም አረንጓዴ ቢጫ ቀይ ክር አይደለም ራዕይ 12 ፥ 10 _ 12 አንገታችንንም መሰዋት ካለብን ስለ ክርስቶስ እንሰዋለን እንጂ ዘማሪዋ ማኅተምሽን ፍቺ በጥሺው ቢሉኝ እኔስ ከነ አንጌቴ ውሰዱት አልኩኝ እንዳለችው ስለሚታሰረው የማኅተም ክር አንገታችንን በጥሱት አንልም ለምን እና ስለ ማን እንደሚሞት ያወቀ ሰው አንገቱ ላይ ስለታሰረ ክር አንገቴን በጥሱት አይልም ይህ አለመረዳትና የድንግዝግዝ ሕይወት ነው መሞት ካለብን ስለ ክርስቶስ እና ስለበጉ ደም ነው የምንሞተው እንደገናም ጴጥሮስም ሆነ ጳውሎስ የተሰቀሉትም ሆነ የተሰየፉት ስለ ተዋሕዶ ሳይሆን ስለ ክርስቶስ ነው ስለዚህ ሰው መሞት ያለበት ተዋሕዶ እያለ ሳይሆን ክርስቶስ እያለ ነው በመሆኑም እነዚህ ግጥሞችም ሆኑ መዝሙሮች በዚህ በተጻፈውና በተብራራው ቃል መሠረት ቢስተካከሉ ተስተካክለውም እስኪወጡ ድረስ ባይዘመሩ መልካም ነው እላለሁ ለምን ብትሉኝ ከሚሰጡት ጥቅም ይልቅ በአመዛኙ ጉዳታቸው አስከፊ ስለሆነ ለሚዘምራቸውም ሆነ በመነባንብ መልክ ለሚያቀርባቸው ሁሉ ከእግዚአብሔር ቃል የወጡ አለሌ ግጥሞች ናቸው ውድ ወገኖቼ እንግዲህ በተረፈ ጌታ ዘመናችሁን ይባርክ በሚቀጥለው የትምህርት ክፍለ ጊዜ እስክንገናኝ ሰላም ሁኑ የምላችሁ ከ Joshua Breakthrough Renewal Apostolic Ministry ቀሲስ አባ ዮናስ ጌታነህ God bless u all http://www.Facebook.com/yonas.asfaw.39 https://www.youtube.com/yF76GIi_rCQ yonasasfaw8@gmail.com

No comments:

Post a Comment