የአገልግሎቱ መሥራች : ----- እንኳን ደህና መጣችሁ ወደ ኦርቶዶክስ ተሃድሶ ሐዋርያዊ አገልግሎት ዌብሳይት አገልግሎቱ የተመሠረተው በአባ ዮናስ ጌታነህ ሐዋርያዊ አገልጋይ ሲሆን አባ ዮናስ ጌታነህ የዚህ የኦርቶዶክስ ተሃድሶ ሐዋርያዊ አገልግሎት መሥራችና መሪ ነው አባ ዮናስ ጌታን ማገልገል የጀመረው በኢትዮጵያ የካላንደር አቆጣጠር ከ1985 - 1996 በኢትዮጵያ ሲሆን ከዚያም ወደ ካናዳ በመምጣት ይህንኑ አገልግሎት ከ1996 - 2013 እስካሁን ድረስ በማገልገል ላይ ይገኛል ጌታ እግዚአብሔር በአባ ዮናስ ልብ ውስጥ ይህንን ይህንን ራዕይ ያስቀመጠው ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ባዘጋጀችው የሰዋስወ ብርሃን መንፈሳዊ ኮሌጅ የኛ ዓመት ተማሪ በነበረበት ጊዜ ነው ከዚያን ጊዜ ጀምሮ በውስጡ ላለው ለእግዚአብሔር ድምጽ ታዞ ይህንን አገልግሎት በዚያው በኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን ውስጥ ለውስጥ በማገልገል ቆይቶ በ1990 ዓመተ ምህረት ከአምስት መነኮሳት ጋር በመሆን በአደባባይ ትልቅ የጀማ ክሩሴድ በኤግዚቢሺን ማዕከል በማዘጋጀትና በመስበክ አገልግሎቱን ይፋ አደረገ ኦርቶዶክስም ከዚያን ጊዜ ጀምሮ እርሱንና ጓደኞች መነኰሳትን የእኛ አገልጋዮች አይደሉም በማለት ትክክለኛ ያልሆነ የውግዘት ደብዳቤ አስተላልፋ ከቤተክርስቲያኒቱ አውግዛ ለይታቸዋለች ከዚያ በኋላ ነው ይሄ አገልግሎት በካናዳ ሀገር ቀጥሎ አሁን የደረሰበት ደረጃ ላይ የደረሰው ይህ አገልግሎት አሁንም ነጻ የሚያወታውን ብቸኛ የኢየሱስ ክርስቶስን የማዳን ወንጌል ለመስበክና የዳኑትንም ሰዎች ተከታትሎ በማስተማር የክርስቶስ ደቀመዝሙር ለማድረግ የታመነና የተዘጋጀ ነው ይህ አገልግሎት አሁንም ነጻ የሚያወጣውን ብቸኛ የኢየሱስ ክርስቶስን የማዳን ወንጌል የሚሰብክና የዳኑትንም ሰዎች ተከታትሎ በማስተማር የክርስቶስ ደቀመዝየሚያደርግ ነው
ምክሐ ዘመድነ: ሃይማኖተ አበው ቀደምት
እመቤታችን ድንግል ማርያምን ምክሐ ዘመድነ (የባሕርያችን መመኪያ) ብሎ ማመስገን ቃለ ሊቃውንት ከመሆኑም በላይ የነገረ ድኅነትን ምስጢር የሚያስረዳ የቀደሙ አባቶቻችን ርትዕት ሃይማኖት መገለጫ መሆኑን በሃይማኖተ አበው ክታባቸው የተደጎሰላቸው ቅዱሳን አባቶች ትምህርት ያስረዳናል። ለማሳያ እንዲሆነን ጥቂቶቹን ብቻ እንመልከት።
ቅዱስ ጎርጎርዮስ
ሰማዕት ዘእንበለ ደም (ያለ ደም ሰማዕት የሆነ) የአርማንያ ኤጲስ ቆጶሳት አለቃ ቅዱስ ጎርጎርዮስ ጌታ ከእመቤታችን በመወለዱ ሰዎች መለኮትን ለማየት መብቃታቸውን አንስቶ ባመሰገነበት ድርሳኑ እንዲህ ብሏል። “ኮነ በአርያም ሰብእ እስከ ኮኑ ሰብአ ድልዋነ ይርአይዎ ለመለኮት እስመ ሶበ ርኢነ ዘመደ ሥጋነ ንሴብሖ ለመለኮተ ወልድ በኂሩቱ ለአብ/ሰዎች መለኮትን ያዩት ዘንድ የበቁ እስኪሆኑ ድረስ በሰው ባሕርይ ተገለጠ፣ በሥጋ ዘመዳችን ሆኖ ባየነው ጊዜ በአብ ቸርነት የወልድን ጌትነት እናመሰግነዋለንና።” (ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘአርማንያ 15:11)
ቅዱስ አትናቴዎስ
ሐዋርያዊ አትናቴዎስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ሥጋን ነፍስን ነስቶ መወለዱን ክደው “ቃል ሥጋ ለመሆን ተለወጠ” በሚል ክህደት የጠፉ መናፍቃንን በገሰጸበት ድርሳኑ ጌታ ከእመቤታችን የእኛን ባሕርይ መንሳቱ የድኅነታችን መሠረት መሆኑን ገልፆ አስተምሯቸዋል። ጌታ በተዋሕዶ ባሕርያችንን ባሕርይው ከማድረጉ በላይ ለሰው ልጅ የተሰጠ ክብርና መመኪያ የለምና። “ለብው ኦ አብዳን ሰሚዐክሙ ቃለ መጻሕፍት ወእመኑ እስመ ሥጋሁ ለእግዚእነ እማርያም እምቅድስት ድንግል ውእቱ ወአኮ እም ካልእ/እናንት አላዋቆች የመጻሕፍትን ቃል ሰምታችሁ ዕወቁ፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተዋሐደው ሥጋ ከቅድስት ድንግል ማርያም እንደሆነ ከሌላ እንዳይደለ እመኑ።” (ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ 30:9)። “ደካማ ባሕርያችንን ለማዳን ወደዚህ ዓለም ስለመጣ” (ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ባስልዮስ 33:35) ከባሕርያችን መመኪያ ከእመቤታችን ሥጋን ነፍስን ነስቶ ተገለጠ።
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ
ፍጡር ለሆነ ለሰው ባሕርይ ከእግዚአብሔር ጋር መዛመድን (በተዋሕዶ መክበርን) የመሰለ ምን ሞገስ አለ? ይህን ክብር ያገኘነው ተስፋ ቅዱሳን አበው በተፈፀመባት በባሕርያችን መመኪያ በድንግል ማርያም ነው። የተወደደ መምህር ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዲህ አለ: “ለቡ ዘተብህለ ወኢተኀሊ ከመ ንስቲት ክብር ይእቲ ዘነሥአ እግዚአብሔር እምኔነ እስመ ኢወሀበ ዘንተ ለመላእክት ወኢህላዌ መላእክት እንተ ተወክፈቶ አላ ህላዌ ዚአነ። …ለዝንቱ ሶበ እዜከሮ ብዙኃ ጊዜያተ አነክር እምኔሁ ወእዴመም ወእኔጽር ብዙኃ ክብራተ ዘአልቦቱ ወሰን ዘረክበ እጓለ እመሕያው ወፍቅረ ዐቢየ ዘኢይትነገር ዘረከበ ህላዌነ ዘእምእግዚአብሔር/ የተነገረውን አስተውል እግዚአብሔር ከእኛ ባሕርይ የተዋሐደው ተዋሕዶ ጥቂት ክብር አይምሰልህ ይህንን ለመላእክት አላደረገውምና፣ የመላእክት ባሕርይም አልተዋሐደችውምና፣ የተዋሐደችው የኛ ባሕርይ ናት እንጂ።…ይህን መላልሼ ባሰብኩት ጊዜ ሰው ያገኘውን ልክ መጠን የሌለውን ፍጹም ክብር ከእግዚአብሔር የተደረገውን ባሕርያችን ያገኘውን ታላቅ ፍቅር አይቼ ከዚህ የተነሣ አደንቃለሁ።” (ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ 62:4-7)
እስራኤል ዘሥጋ ሙሴ ስለ እነርሱ ከእግዚአብሔር ጋር ደጋግሞ በመነጋገሩ የሚመኩበት ከሆነ እኛማ በዘመነ ሐዲስ የምንገኝ፣ በሐዲስ ተፈጥሮ የእግዚአብሔር ልጆች የመባልን ጸጋ ያስገኘችልንን የባሕርያችን መመኪያ እመቤታችን ድንግል ማርያምን የቱን ያህል ማክበር ይገባን ይሆን?! የዘመነ ብሉይ ቅዱሳት አንስት (ሴቶች) እንደ ሐና እመ ሳሙኤል ምድራውያን ካህናትን ስለወለዱ እስራኤል ያከበሯቸው ከሆነ እኛማ መፈታትን ያገኘንበት ልዩ ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስን ያዛመደችንን ድንግል ማርያምን ምን ብለን ብናመሰግናት ይበቃን ይሆን?! በሥጋ ማርያም በመገለጡ፣ ፍጹም እግዚአብሔር፣ ፍጹም ሰው (አብሲዳማኮስ፣ የሐዲስ ኪዳን መካከለኛ) በመሆኑ ማለፍ መለወጥ የሌለበት የዘለዓለም ሊቀ ካህናት ሆኗልና።
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ይህንን ሲያስረዳ እንዲህ አለ: “ወአኮ ይኩነነ እኅወ ባሕቲቶ አላ ተሣሃለነ ፈድፋደ ወፈቀደ ዓዲ ይኩነነ ሊቀ ካህናት ለኀበ አብ ከመ ይስረይ ኃጢአተነ፣ ወበእንተ ዝንቱ ወሰከ በዲበ ነገሩ ወይቤ ከመ ይኩኖሙ መሐሬ በኵሉ ምእመን ሊቀ ካህናት ለመንገለ እግዚአብሔር ከመ ይስረይ ኃጢአተ ሕዝብ።/ሰው የሆነም ዘመድ ሊሆነን ብቻ አይደለም፣ ፈጽሞ ይቅር አለን። ኃጢአታችንን ለማስተስረይ ከአብ ጋር ለማስታረቅ ሊቀ ካህናትም ይሆነን ዘንድ ወደደ እንጂ። ስለዚህም ሰዎችን ሊመስላቸው ይገባል ባለው ነገሩ ላይ ጨምሮ በሁሉ አዛኝ የሕዝቡንም ኃጢአት ለማስተስረይ በእግዚአብሔር ዘንድ የታመነ አስታራቂ ይሆናቸው ዘንድ ነው።” (ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ 62:13)
ቅዱስ ኤራቅሊስ
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እኛን ለማዳን ከባሕርያችን መመኪያ ከድንግል ማርያም ሥጋና ነፍስን ስለነሳ አማኑኤል (እግዚአብሔር ከእኛ ጋር) ተባለ። ፍጹም ሰው በመሆኑም የወደቀ ባሕርያችንን ወደቀደመ ክብሩ መለሰልን። ይህን አምላካዊ ምስጢር ለማድነቅ ቃላት ያጠረው ቅዱስ ኤራቅሊስ እንዲህ አለ: “ኦ ከርሥ ዘተጽሕፈ በውስቴታ መጽሐፈ ግዕዛን እምግብርናት ለኩሉ ሰብእ!?…ኦ መቅደስ ዘኮነ ባቲ እግዚአብሔር ካህነ/ ለሰው ሁሉ ከመገዛት የነፃነት መጽሐፍ የተጻፈባት ማኅፀን ወዮ እንደምን ያለች ናት!?…እግዚአብሔር ያገለገለባት መቅደስ ወዮ እንደምን ያለች ናት?!” (ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ኤራቅሊስ 48:15-17) ስለሆነም ዕለት ዕለት በጸሎተ ቅዳሴ በካህኑ መሪነት “የባሕርያችን መመኪያ ሆይ ደስ ይበልሽ” እያልን እናመሰግናታለን።
የባሕርያችን መመኪያ ሲባል ምን ማለት ነው?
ባሕርይ የምንነት መገለጫ ነው። የሰው ልጅ ከአራት ባሕርያተ ሥጋና ከሦስት ባሕርያተ ነፍስ በእግዚአብሔር አምሳል የተፈጠረ ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ “እግዚአብሔርም አለ ሰውን በመልካችን እንደ ምሳሌአችን እንፍጠር” እንዲል፡፡ (ዘፍ. 1፡26) ሰው በሥጋ ባሕርይ ውኀነትን፣ እሳትነትን፣ ነፋስነትንና መሬትነትን ሲይዝ በነፍስ ባሕርይ ደግሞ ልባዊነትን (ማስተዋልን)፣ ነባቢነትንና (መናገርን) ሕያውነትን (ለዘላለም መኖርን) ይዟል፡፡ የእነዚህ ባሕርያት ፍጹም ተዋሕዶ ሰብአዊ ባሕርይ ይባላል፡፡ ይህ የሰውነት ባሕርይ በውጫዊ ነገር መለዋወጥ በኑሮ ጉስቁልና ወይም ምቾት አይቀየርም።
ሰው በባሕርይው ባለ ነፃ ፈቃድ ተመሥርቶ ጽድቅንም ኃጢአትንም ማድረግ ይችላል። በአባታችን አዳምና በእናታችን ሔዋን ምክንያት የመጣው ሕገ እግዚአብሔርን መተላለፍም ይህን እውነታ በግልጥ ያስረዳናል። አዳምና ሔዋንም በነፃ ፈቃዳቸው ተመርተው በፈጸሙት መተላለፍ የሰው ባሕርይ (ሰውነት) ከነበረበት የቅድስናና የንጽሕና አኗኗር ተለይቶ ነበር፡፡ ባሕርይው ጎስቁሎ፣ ልጅነቱን አጥቶ ነፃነቱንና ሕያውነቱን አጥቶ በሞት መዳፍ ተይዞ ነበር። ይህ በአዳምና በሔዋን መተላለፍ ምክንያት ወደ ዓለም የገባው ኀጢአትና ውጤቱ ከእነርሱ በባሕርይ ለሚወለድ ሁሉ ተላለፈ። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “…ኃጢአት በአንድ ሰው ወደ ዓለም ገባ በኃጢአትም ሞት፣ እንደዚሁም ሁሉ ኃጢአትን ስላደረጉ ሞት ለሰው ሁሉ ደረሰ…ነገር ግን በአዳም መተላለፍ ምሳሌ ኃጢአትን ባልሠሩት ላይ እንኳ ከአዳም ጀምሮ እስከ ሙሴ ድረስ ሞት ነገሠ፤ አዳም ይመጣ ዘንድ ላለው ለእርሱ አምሳሉ ነውና” እንዳለ፡፡ ሮሜ. 5፡ 12-14። ይህ የአዳምና የሔዋን በደልም ጥነተ አብሶ ይባላል። ከእነርሱ የሚወለዱ ሁሉ በጥንተ አብሶ የሚያዙ ሆኑ።
እግዚአብሔር ከዚህ ያድናቸው ዘንድ አዳምና ልጆቹ በዘመናት ሁሉ ወደ እግዚአብሔር ሲጸልዩ ኖሩ። እግዚአብሔርም ቃል ገባላቸው። ቃል ኪዳኑ እስኪፈፀም ድረስም ላደፈው ባሕርይና ለጎሰቆለው ሕይወት መታደስ ምክንያት ከእግዚአብሔር ጋር የሚያገናኛቸውን ድልድይ ሲጠባበቁ ኖሩ። ይህች ድልድይ ወይም መሰላል የኾነችም እመቤታችን ድንግል ማርያም ነች፡፡ ለዚያም ነው ‘የባሕርያችን መመኪያ’ የምንላት። እርስዋ በቅድስና ተጠብቃ በውስጥ በአፍኣ በነፍስ በሥጋ በንጽሕና ተሸልማ የሰውን ባሕርይ ወደ ቀደመ ክብሩ ለመመለስ ከባሕርያችን የተገኘች ምክንያተ ድኅነት ናትና፡፡
ይህ የእመቤታችን ድልድይነት ከዘመነ ብሉይ እስከ ዘመነ ሐዲስ በብዙ ሕብረ አምሳል የተገለጠ፣ ትንቢት የተነገረለት ሱባኤ የተቆጠረለት ነው፡፡ አባታችን ያዕቆብ ሰው ከእግዚአብሔር በተለየበት፣ እግዚአብሔርም ከሰው በረድኤት በራቀበት ዘመን መጭውን የድኅነት ብሥራት በሕልም አየ። በሕልሙ የወርቅ መሰላል ከምድር እስከ ሰማይ ተተክሎ እግዚአብሔር በላዩ ቆሞበት መላእክት በመሰላሉ ሲውጡ ሲወርዱ አየ። “ሕልምንም አለመ፤ እነሆም መሰላል በምድር ላይ ተተክሎ፣ ራሱም ወደ ሰማይ ደርሶ፣ እነሆም የእግዚአብሔር መላዕክት ይወጡበት ይወርዱበት ነበር፤ እነሆም እግዚአብሔር በላይ ቆሞበት ነበር” እንዲል (ዘፍ. 28፡12-13)፡፡ ይህች አባታችን ያዕቆብ በሕልሙ ያያት መሰላል የድንግል ማርያም ምሳሌ ነበረች፡፡ ይህም ጌታ ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነስቶ በማኅፀኗ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን አድሮ ከእመቤታችን በቤተልሔም በተወለደ ዕለት መላዕክት ከእረኞች ጋር በአንድነት ባመሰገኑበት ጊዜ ተፈጽሟል፡፡ (ሉቃስ 2፡ 8-14)።
የብህንሳው ኤጲስ ቆጶስ አባ ሕርያቆስም በቅዳሴ ማርያም ድርሰቱ “ወዮ ይህ ነገር ዕጹብ ድንቅ ነው የቀደሙ አባቶች ከሞት ወደ ሕይወት የተሸጋገሩብሽ ድልድይ ሆይ፣ ከምድር እስከ ሰማይ የምትደርሽ መሰላል ሆይ፣ የፍጥረት ሁሉ መጀመሪያ በአንቺ ታደሰ፡፡ ከገነት በተሰደደ ጊዜ የአዳም ተስፋው አንቺ ነሽ” በማለት አመስግኗታል፡፡ (ቅዳሴ ማርያም ቁጥር 30)። ስለዚህም እመቤታችንን የባሕርያችን መመኪያ እንላታለን፡፡
እመቤታችንን የባሕርያችን መመኪያ ያስባሏት ዋና ዋና ነጥቦች
የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ክብር ከፈጣሪ በታች ከፍጡራን ሁሉ በላይ ስለሆነ ሙሉ ምስጋናዋን አንሥተን መፈጸም አይቻለንም፡፡ ነገር ግን የባሕርያችን መመኪያ ከሚያስብሏት መጽሐፋዊ ምክንያቶች የተወሰኑትን እናያለን፡፡
አምላክ የሰውን ባሕርይ በእርሷ ስለተዋሐደ
እግዚአብሔር የወሰነው ዘመን ደርሶ የገባውን የምሕረት ቃል ኪዳን ሊፈጽም በወደደበት ወቅት ማደርያው ትሆነው ዘንድ የመረጣት ድንግል ማርያም ነች፡፡ እርሷም ዓለም ሳይፈጠር ለዓለም ድኅነት ምክንያት ትሆን ዘንድ እግዚአብሔር የቀደሳት በውስጥ በአፍኣ፣ በነፍስ በሥጋ ፍጽምት ቅድስት ሆና የተገኘች ናት። ይህችውም ከአዳም ዘር የተወለደች እግዚአብሔር ለድኅነተ ዓለም ያዘጋጃት ሰዋሰወ ብርሃን (የብርሃን መሠላል) ናት። እግዚአብሔር ሰውን ለማዳን የሰውን ባሕርይ እንጅ የመላእክትን ባሕርይ አልፈለገምና፡፡ ለዚያም ነው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የመዳናችን ራስና ፈጻሚ ስለሆነው ስለ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተናገረበት አንቀጽ “የአብርሃምን ዘር ይዞአል እንጅ የያዘው የመላእክትን አይደለም” ያለው፡፡ (ዕብራ. 2፡16)
ስለዚህ የባሕርይ አምላክ የሰውን ባሕርይ ተዋሕዶ ከነፍስዋ ነፍስ፣ ከሥጋዋም ሥጋ ነስቶ ተወለደ። በተዋሐደው የሰው ባሕርይም እንደ ሕፃን አደገ። ወደ ግብፅ ተሰደደ። በዮርዳኖስ ተጠመቀ። ሦስት ዓመት ከሦስት ወር በምድር ላይ ተመላልሶ ወንጌልን አስተማረ። በተዋሐደው ሥጋ መከራን ተቀበለ፣ ተሰቀለ፣ ሞተ፣ ተቀበረ። በሦስተኛውም ቀን ከሙታን ተለይቶ ተነሳ። በአርባኛውም ቀን ወደ ሰማይ ዐረገ። በአባቱም ቀኝ ተቀመጠ። ከእንዲህ እናስተውል በአባቱ ቀኝ የተቀመጠው ወልድ ዋሕድ እየሱስ ክርስቶስ ከሁለት ባሕርይ አንድ ባሕርይ፣ ከሁለት አካል አንድ አካል የሆነው በተዋሕዶ የከበረው ከእርሷ ተወልዶ ነው። በእትሷ የተፈፀመው የተዋሕዶ ምሥጢር ሰው (የሰው ባሕርይ) አምላክ አምላክም (መለኮት) በተዋሕዶ ሰው የሆነበት ነውና በእውነት የባሕርያችን መመኪያ ናት።
በባሕርያችን ያደረ እርግማን በእርሷ ስለራቀልን
ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ “ስለ ሔዋን የገነት ደጅ ተዘጋ፤ ዳግመኛም ስለ ድንግል ማርያም ተከፈተልን” (የሐሙስ ውዳሴ ማርያም) በማለት የእመቤታችንን ምክንያተ ድኅነትነት አስረድቷል፡፡ የውዳሴ ማርያም መተርጉማንም ሲያስተምሩ እናታችን ሔዋን የሞት ምክንያት ስለ ተባለች ወቀሳ፣ ከሰሳ ይበዛባት ነበር፡፡ በሔዋን አንፃርም ሴቶች ሁሉ የስሕተት ምክንያት እንደ ሆኑ አድርገው የሚያስቡ ብዙዎች ነበሩ፡፡ ወንዶችም ይህን እየጠቀሱ በሴቶች ላይ ይመኩባቸው ነበር፡፡ አሁን ግን ድኅነት በእመቤታችን በኩል ሆኗልና የወንዶች ትምክህት ቀርቷል፡፡ እመቤታችንም ቅዱስ ገብርኤል የድኅነት ምክንያት መሆኗን ባበሰራት ሰዓት የሔዋንን ጸሎትና ልመና በማስታወስ “ነፍሴ ጌታን ታከብረዋለች….የባርያይቱን መዋረድ ተመልክቷልና” (ሉቃ. 1፡47-48) በማለት የሔዋን ምክንያተ ሞት መሆን በእርሷ ምክንያተ ድኂን መሆን መታደሱን ተናግራለች፡፡
በንጽሐ ባሕርይዋ የሰውን ንጽሐ ባሕርይ ስለምታሳይ
የሰው ልጅ ሕግን ተላልፎ በመበደሉ (ጥንተ አብሶ) እግዚአብሔር ተለየው፣ ከእግዚአብሔርም ተለየ፡፡ በራሱ ትሩፋትም ወደ እግዚአብሔር መመለስና መዳን አልተቻለውም። ስለዚህ ድካሙን ያግዝለትና ድኅነቱን ይፈጽምለት ዘንድ ጌታ ለአዳም ቃል ኪዳን ገባለት። ቃል ኪዳኑም ከልጅ ልጅህ ተወልጄ በመስቀል ተሰቅዬ ሞቼ አድንሃለሁ የሚል ነበር። ለዚህ ቃል ኪዳን ፍጻሜም ምክንያት ትሆን ዘንድ እመቤታችንን በንጽሕና ፈጥሮ፣ ከጥንተ አብሶ ጠበቃት። በዘመነ ብሉይ የነበሩ ሁሉ በዚህ በደል የተያዙ ነበሩና (ሮሜ. 5፡12-14)። ሁሉም ከኃጢአት በታች እንደነበሩም ተጠቅሷል፡፡ ለምሳሌ ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ “ሁላችን እንደ ርኩስ ሰው ሆነናል፣ ጽድቃችንም እንደ መርገም ጨርቅ ነው” ብሏል፡፡ (ኢሳ. 64፡ 6)
ነቢዩ ኢሳይያስ ከላይ የተጠቀሰውን የተናገረው ከሕግ በታች ይኖርበት ከነበረው ዘመነ ብሉይ ወደ ዘመነ ሐዲስ ለመሸጋገር የጌታን መወለድ (አስተርዕዮ) በተማጸነበት የትንቢቱ ክፍል ነው፡፡ ምዕራፉን ሲጀምርም “ሰማዮችን ቀድደህ ምነው ብትወርድ!” (ኢሳ. 64፡1) ብሏል፡፡ ይህን የተናገረ ኢሳይያስ በዘመነ ብሉይ ከነበሩ ሰዎች ሁሉ ለይቶ እመቤታችን ድንግል ማርያም በጥበበ እግዚአብሔር ከመጀመሪያው በደል (ጥንተ አብሶ) ተጠብቃ መቀመጧን በትንቢት መነጽር ተመልክቶ ነበር፡፡ ይህንንም ሲያስረዳ “የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ዘርን ባያስቀርልን ኖሮ፣ እንደ ሰዶም በሆንነ እንደ ገሞራም በመሰልን ነበር” (ኢሳ. 1፡9) ብሏል፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞንም በመዝሙሩ “ወዳጄ ሆይ ሁለንተናሽ ውብ ነው ነውርም የለብሽም” (መኃልይ. 4፡7) በማለት በምሳሌ የእመቤታችንን ፍጹም ንጽሕና ተናግሯል፡፡ እንደ ሰዶምና ገሞራ ሰዎች ጠፍተን፣ በኃጢአት ተይዘን እንዳንኖር የድኅነት ምክንያት የሆነች፣ ንጹሕ ዘር የተባለች፣ የባሕርያችን መመኪያ የሆነች እመቤታችንን ከአዳም ጀምሮ እስከ ኢያቄም አብራክ ያስቀረልን እግዚአብሔርን እናመሰግነዋለን፡፡
ይህን የእመቤታችንን ፍጹም ንጽሕና ባሰብን ጊዜ እርሷ እንደ እኛ ከሰው ባሕርይ ተፈጥራ ንጽሐ ሥጋና ንጽሐ ልቦናን አስተባብራ የያዘች በመሆኗ ከአዳም ልጆች ከአንስተ ዓለም እርሷን መርጦ የሰጠንን አምላክ እናመሰግናለን። እርሷንም በቅድስናዋ መዓዛ ከርኵሰታችን ሽታ ታነጻን ዘንድ እንለምናታለን። እርሷን ምሳሌ አድርገን ሰውነታችንን ለእግዚአብሔር ቅዱስ ማደርያው ይኾን ዘንድ በንጽሕና እንጠብቀዋለን። እርስዋ የንጽሕናና የቅድስና አብነት ሆናልናለችና፡፡ ስለዚህም ነው ቅዱስ ኤፍሬም በቀዳሚት ሰንበት ምስጋናው “ከዳዊት ዘር የተገኘሽ ባሕርይ /ዘር/ አንቺ ነሽ፡፡ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በሥጋ ወልደሽልናልና” በማለት ያወደሳት፡፡
በትንሣኤዋ ለሰው ልጆች የክብር ትንሣኤ ማሳያ ስለሆነች
ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ትንሣኤ ባስረዳበት መልእክቱ “አሁን ግን ክርስቶስ ላንቀላፉት በኩራት ሆኖ ከሙታን ተነሥቶአል” (1ኛ ቆሮ. 15፡20) ብሏል፡፡ የጌታ ትንሣኤ ሞት የተሸነፈበት ትንሣኤ ስለሆነ የሰው ልጆች በሙሉ በዳግም ምጽአት እርሱን አብነት አድርገን የማይፈርስ የማይበሰብስ አካል ይዘን እንነሣለን፡፡ ይሁን እንጂ አንዳንዶች ይህን የትንሣኤያችን በኩር የሆነው የክርስቶስ ትንሣኤ ሲነገራቸው “እርሱ በገዛ ሥልጣኑ ስለ ተነሣ እኛ ግን እንዴት እንነሣለን?” በማለት ታላቁ የእምነታችን መሠረት የሆነውን ትንሣኤ ሙታንን የሚጠራጠሩ በየዘመናቱ አሉ። የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤ ለእነዚህ ወገኖች በእውነት ትንሣኤ ሙታን እንዳለ አንድ ማሳያ ነው።
በቤተ ክርስቲያን ታሪክ እንደሚታወቀው፣ ሁሉም ቀደምት አብያተ ክርስቲያናት እንደሚስማሙበት፣ በሊቃውንት አበው እንደተጻፈው እመቤታችን ድንግል ማርያም በሥጋ ባረፈች ጊዜ ጌታ ሥጋዋን ለመፍረስ ለመበስበስ አልተወውም፡፡ ይልቁንም የከበረ ሥጋዋን ለማቃጠል ከተሰበሰቡ ሰቃልያነ እግዚእ አይሁድ በጥበብ አስጥሎ ቅዱሳን ሐዋርያት ከቀበሯት በኋላ ጌታ የከበረ ሥጋዋን በገነት ከዕፀ ሕይወት ሥር አስቀመጠው እንጅ፡፡ የእውነተኛው ዕፀ ሕይወት (የሕይወት ፍሬ) መገኛ የሆነች የባሕርያችን መመኪያ የድንግል ማርያም የከበረ ሥጋ በሕይወት ዛፍ ስር ተቀመጠ፡፡ ትንሣኤና ዕርገቷንም በሱባኤ ይማጸኑ ለነበሩ ለቅዱሳን ሐዋርያት በልዩ ልዩ ተአምራት ገለጠላቸው፡፡ ድንግል ማርያም በተፈጥሮ እንደ እኛው ምድራዊት ስትሆን በልጅዋ ሥልጣን ሞትን ድል አድርጋ በመነሣት ወደ ሰማይ ዐረገች። ስለሆነም ትንሣኤዋ ለምድራውያን ሰዎች የማይቀር ትንሣኤ ማሳያ ሆነልን፡፡
የሰው ባሕርይ በሔዋን የሞት ምክንያትነት ሞት፣ ጉስቁልና እና መፍረስ መበስበስ አግኝቶት ነበር። አማኑኤል የተባለ የተወደደ ልጇን በወለደችልን በድንግል ማርያም የሕይወት ምክንያትነት ደግሞ እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ሆነ። ሔዋን ለሞት፣ ድንግል ማርያም መፍረስ መበስበስ ለሌለበት ሕይወት ከሰው ልጆች ሁሉ የመጀመሪያ ሆኑ። ሔዋን በበደሏ፣ በትዕቢት ባለመታዘዟ ለሰይጣን መገዛትን ወደ ሰው ባሕርይ ለማምጣት የመጀመሪያዋ እንደነበረች ንጽሕት ድንግል ማርያም እግዚአብሔርን ባስደሰተ ቅድስናዋ፣ በፍጹም ትህትና በመታዘዟ በልጇ ሥልጣን ሞትን፣ መፍረስ መበስበስን አሸንፈው ለዘለዓለም በሕይወት ሊኖሩ የክብር ትንሣኤን ከሚነሱ ሁሉ ቀድማ በመነሣቷ የባሕርያችን መመኪያ መሆኗ ታወቀ።
የባሕርያችን መመኪያ ስለሆነች በጸሎታችን እንማጸንባታለን
እስራኤል ዘሥጋ ከእግዚአብሔር ምሕረትን ሲፈልጉ የሚመኩባቸውን ቅዱሳን አበው የአብርሃምን፣ የይስሐቅን፣ እስራኤል የተባለ የያዕቆብን ስም ይጠሩ ነበር፡፡ እግዚአብሔርም ይራራላቸው ነበር፡፡ ለምሳሌ ሊቀ ነቢያት ሙሴ አግዚአብሔር በእስራኤላውያን ተቆጥቶ ሊያጠፋቸው ባለ ጊዜ ለሕዝበ እስራኤል ምሕረትን የለመነው የእነዚህን ቅዱሳን አበው ስም በአማላጅነት ጠርቶ ነበር፡፡ “ሙሴም በእግዚአብሔር በአምላኩ ፊት ጸለየ፤ አለም፡፡…ዘራችሁን እንደ ሰማይ ከዋክብት አበዛለሁ፣ ይኽችንም የተናገርኋትን ምድር ሁሉ ለዘራችሁ እሰጣታለሁ፣ ለዘላለምም ይወርሷታል ብለህ በራስህ የማልህላቸውን ባርያዎችህን አብርሃምንና ይስሐቅን እስራኤልንም አስብ”። ዘጸ. 32፡11-13።
የዘመነ ብሉይ ምዕመናን በታላላቅ አርዕስተ አበው ቅዱሳን በአብርሃም፣ በይስሐቅና በያዕቆብ ቃል ኪዳን ተመክተው እግዚአብሔርን ይለምኑት እንደነበር እኛም የባሕርያችን መመኪያ በሆነች በድንግል ማርያም ጸሎትና ቃል ኪዳን እንታመናለን። በምርኮ የነበሩ አይሁድ በምድራዊ ንጉሥ ቤተ መንግስት ባለሟልነት ባላት በወገናቸው በደካማዋ በአስቴር ተመክተው ከሞት ፍርድ ካመለጡ (መጽሐፈ አስቴር ምዕራፍ 4-ምዕራፍ 8) እኛማ አምላክን በወለደች፣ በንጽሕና በቅድስና ባጌጠች፣ የሰማያዊ ንጉሥ የክርስቶስ ምድራዊት ቤተ መቅደስ በሆነች በባሕርያችን መመኪያ በእመቤታችን ድንግል ማርያም የመመካታችን ዋጋ ምን ይሆን!? ስለሆነም እስራኤል ዘነፍስ የምንባል የሐዲስ ኪዳን ምእመናን ከቅዱሳን ሁሉ በምትበልጥ፣ የባሕርያችን መመኪያ በሆነች በድንግል ማርያም ስም ልጇ ወዳጇን ኢየሱስ ክርስቶስን እንማጸነዋለን፡፡ ዘወትርም በቅዳሴና በጸሎት “በእንተ ማርያም መሐረነ ክርስቶስ/ ክርስቶስ ሆይ ስለ እናትህ ስለ ማርያም ብለህ ይቅር በለን” እያልን እንለምነዋለን፡፡ እርሱም ይታረቀናል፡፡
ቅዱሳት መጻሕፍትን ባለማወቅ ትስታላችሁ!
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በጥራዝ ነጠቅ የቅዱሳት መጻሕፍት ንባብ ተነሥተው ትንሣኤ ሙታን የለም የሚሉ ሰዱቃውያንን ሲገስፅ “መጻሕፍትንና የእግዚአብሔርን ኀይል ባለማወቅ ትስታላችሁ” (ማቴ 22:29) ብሏቸው ነበር። ቅዱሳት መጻሕፍትና ቅዱሳን ሊቃውንት በአንድነት ተስማምተው ድንግል ማርያምን “ወላዲተ አምላክ ማእምንት/የታመነች አምላክን የወለደች”፣ “ምክሐ ዘመድነ/የባሕርያችን መመኪያ” በማለት ያመሰግኗታል። የቅዱሳት መጻሕፍትን ምሥጢር ለሚረዳ ሰው እነዚህ ምስጋናዎች ጌታ እኛን ያዳነበትን አምላካዊ ጥበብ የሚያስረዱ መሆናቸውን ይገነዘባል።
ስለ ድንግል ማርያም ክብር፣ አማላጅነት፣ ትንሣኤና ዕርገት ቤተ ክርስቲያን የምታስተምረው ንጹሕ ሐዋርያዊ ወንጌልም ከውድቀት የተነሣ የሰው ባሕርይን የሚመለከት፣ የእግዚአብሔር ቸርነት፣ ለሰው ልጅ የሰጠው መጠንና መመርመር የማይቻል ጸጋ ማሳያ መሆኑን ይረዳል። ይሁንና የነገረ ድኅነትን ትምህርት ባለማወቅ የሚቆነጻጽሉ፣ የድንግል ማርያምን ክብር የማይረዱ ሰዎች ምክንያተ ድኂን (የድኅነት ምክንያት) መሆኗን መረዳት ሲከብዳቸው እናስተውላለን። ባለማወቅና በድፍረት ተሞልተውም የባሕርያችን መመኪያ የእመቤታችንን የድኅነት ምክንያትነት ያቃልላሉ። በአንፃሩ ደግሞ የሔዋንን የሞት ምክንያትነት ግን መረዳት አይከብዳቸውም። ቅዱሳት መጻሕፍትን ባለማወቅ ስተዋል፣ ይስታሉ።
ከቅዱሳን ሐዋርያት ርትዕት ሃይማኖትን የተቀበለች ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን ግን የእመቤታችንን የድኅነት ምክንያት መሆን ዘወትር ታስባለች፣ በጸሎቷም ታሳስባለች። በሔዋን አለመታዘዝ፣ ሕግን መተላለፍ ሞት ወደ ዓለም እንደመጣ በእመቤታችን መታዘዝ፣ ሕግን መፈጸም ሕይወት ክርስቶስ ወደ ዓለም መጥቷልና እመቤታችንን “የባሕርያችን መመኪያ” ብለን እናመሰግናታለን።
ከጥሩ ምንጭ ቀድቶ ቃለ እግዚአብሔርን መረዳት የከበዳቸው ወገኖቻችን “የባሕርያችን መመኪያ” የሚለውን የቅዱሳት መጻሕፍትን ትኩረት (theme) መረዳት ቢችሉ ወደ ርትዕት ሃይማኖት በተመለሱ ነበር። ይሁንና አንዳንዶቹ ባለማወቅና በትዕቢት በማያውቁት ጉዳይ ራሳቸውን “መምህራን” እያሉ ጠማማ ትምህርትን ያስተምራሉ። ይህን የሚያደርጉት ጥሩ ምንጭ በሌለበት የሚኖሩት ብቻ አይደሉም። የሕይወት ውኃ ምንጭ በሚፈልቅባቸው የቤተ ክርስቲያን ዐውደ ምሕረቶች ራሳቸውን ሾመው፣ የቤተ ክርስቲያናችንን ሥርዓት በሚያናንቅ፣ የምዕራባውያንና ሌሎች ምስራቃውያን ሴሚናሪዎችን ልማድ በመከተል ጌታ በወንጌል (ማቴ 23) የገሰፃቸውን ፈሪሳውያንን በሚያስንቅ ግብዝነት፣ በተገዛ ቀሚስና ሀብል፣ ማዕረግ አልባ በሆኑ በሐሰትና በማጭበርበር በተሰበሰቡ የማዕረግ ስሞች ተከልለው ኦርቶዶክሳዊውን ዐውደ ምሕረት ከአባቶቻችን ከተረከብነው ኦርቶዶክሳዊ ትምህርት፣ ትውፊትና ላህይ ለይተው ርካሽ የጭብጨባና የእንቶ ፈንቶ ዐውድ የሚያደርጉትንም ይመለከታል።
እነዚህ ከምንጩ የተለዩ ሰዎች የቤተ ክርስቲያን ምልክት ተደርገው “ዕንቁ፣ ብርቅዬ” መባላቸው በእውነተኛው የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ላይ በአላዋቂ ልብስ ሰፊ እንደተደረተ መጋረጃ ይመስላሉ። ቤተ ክርስቲያን ልትመዘንበት በሚገባው በእውነተኛ አስተምህሮዋ ሳይሆን በምንፍቅና ወይም ለመወደድና ለንግድ ተብለው በሚቀርቡ ሰዎች የለብ ለብ (simplistic) አስተምህሮ እንድትታይ ያደርጋሉና። በዚህም ምክንያት ብዙዎች የቤተ ክርስቲያንን ዕንቍ ትምህርት ሳያገኙ ይቀራሉ። ስለሆነም ቀላል የማይባል ምዕመን ከቤተ ክርስቲያን ጥልቅ አስተምህሮ ባለማወቅ እየተለየ፣ ልቡናውን ከፍ ከፍ አድርጎ ስለ “ባሕርያችን መመኪያ” ከማሰላሰል ይልቅ ዲያብሎስ ትንንሾችን ለመጣል ባጠመደው እንቅፋት እየተጠለፈ ስለ ምልጃ፣ ስለ ትንሣኤና ዕርገት “ሀ” ብሎ የሚነታረክ ሆኗል። ለዚህ መሰል ትውልድ የአባታችን ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ተግሳፅ የሚጠቅም ይመስለናል።
ተግሳፅ ዘአባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ
ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ የቅዱሳት መጻሕፍትን ምሥጢር ሳይረዱ እግዚአብሔር ወልድ ኢየሱስ ክርስቶስ ያለ ምንታዌ (ከተዋሕዶ በኋላ የሥጋና የመለኮት ባሕርይ ሳይነጣጠሉ፣ ሳይከፋፈሉ) ባሕርያችንን ባሕርይው ማደረጉን በመካዳቸው፣ እመቤታችን ድንግል ማርያምም የባሕርያችን መመኪያ መሆኗን በማቃላላቸው ንስጥሮሳውያንን በገሰፀበት የመጽሐፈ ምሥጢር ንባብ ያስተማረው ትምህርት በዘመናችን ላሉ የድንግል ማርያምን ክብር ባለማወቅ ለሚያሳንሱ ሰዎች የሚስማማ ነው።
አባ ጊዮርጊስ እንዲህ አለ: “በተከማቸ መጽሐፍ ውስጥ የተሸሸገ ዕንቍን ልቡ የታወረ አያየውም። በነቢያትና በሐዋርያት አፍ የመለኮት ድምፅ ይጮሀል ኅሊናው በደነቈረ ሰው ጆሮ ግን አይገባም። የብረት መዝጊያ ቢበረታም በብረት ሰሪው እጅ ይከፈታል፣ የናስም መቀርቀሪያዎች በማንጠሪያ እሳት ይቀልጣሉ፣ የዝንጉዎችን ልብ ግን በጥበብ ቃልም ቢሆን፣ በመጻሕፍትም ቃል ቢሆን ሊከፍተው የሚችል የለም። መጻሕፍትን ማንበብ በሰነፍ አፍ ውስጥ እንደ ነፋስ መንቀሳቀስ ነው፣ ስላነበባት ይመካል፣ በውስጧ ያለውን ግን አያውቅም። የተዘጋን የንጉሥ ቤት ሳጥኖችን የሚያድን ወደ ውስጧ ግን ያልገባን ሰው ይመስላል። ስለነገሥታት ገንዘብ ለሚጠይቀው ሰው ምን ይመልስለታል?።” (መጽሐፈ ምሥጢር የጌና ምንባብ ቁጥር 33)
እንግዲህ እኛስ ምን እንላለን? የቅዱሳት መጻሕፍትን ምሥጢር መረዳት አቅቷቸው በስህተት ጎዳና በድፍረት የሚራመዱትን አላዋቂዎች ምን እንላቸዋለን? ተማሪዎች ነን ቢሉ የቅዱሳት መጻሕፍትን በር ከፍተው እንዲገቡ፣ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስም እንዲመራቸው፣ ማስተዋልን እንዲያድላቸው እንለምንላቸዋለን። የሚያሳዝነው አላዋቂነታቸው በግልጽ እየታየ ራሳቸውን “መምህራን” የሚሉት ይበዛሉ። እነዚህን ለመገሰፅ አሁንም ከአባታችን ጊዮርጊስ ዘጋሰሥጫ ቃል ተውሰን እንወቅሳቸዋለን፣ እንዲመለሱ እናሳስባቸዋለን።
“መጻሕፍትን ከማወቅ የተራቆቱ ሲሆኑ መምህራን የሚባሉ በከበረ ደንጊያ ካጌጡ በወርቅም ቅጠል ከተለበጡ፣ ቀለም በተነከሩ ልብሶች ከተሸፈኑ፣ በሐር ምንጣፍም ላይ ከተቀመጡ ውስጣቸው ግን ከተቆረጡ እንጨቶች፣ ከረከሱም የእንስሳ አጥንቶች ከተሠሩ ዕጣንና ሽቱ ከሚያጥኑአቸው፣ ነገር ግን የዕጣኑ መዓዛ በአፍንጫቸው ከማይገባ፣ ከመሥዋዕታቸው ስብ ከማይበሉ፣ ከወይን ጭማቂአቸውም ከማይጠጡ፣ የሚያምንባቸውን ከማይረዱት፣ በሚገፉአቸውም ላይ ክፉ ከማያደርጉ፣ በከንቱም አማልክት ከሚባሉ የአሕዛብ ነገሥታት ጣዖታት ከአዛጦን ሰዎች ዳጎንና አጵሎን ያልተሻሉ ናቸው። እነርሱ የእግዚአብሔርን ቃል የተጠሙ ሲሆኑ በከንቱ መምህራን የሚባሉ እኒህም እንዲሁ ናቸው፣ ወደነርሱ የመጣውን እንግዲህ እንዴት ያረኩታል? ቢያጠጡትም የደፈረሰውን ውኃ ከነቢያትና ከሐዋርያትም ምንጭ ያልተቀዳውን የተበላሸ ውኃ ያጠጡታል።” (መጽሐፈ ምሥጢር የጌና ምንባብ ቁጥር 34-35)
እንግዲህ እኛም እያንዳንዳችን ራሳችንን እንመርምር። ከእውነተኛ መምህራን ተምረን የባሕርያችንን መመኪያ እንወቅ እንጂ በሐሰተኛ መምህራን ማደናገሪያ ተታለን ከርትዕት ሃይማኖት የተለየን አንሁን። የንጽሕና አብነት የምትሆን፣ በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናች፣ የባሕርያችን መመኪያ የሆነች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን አብነት አድርገን በመንፈሳዊ ተጋድሎ ለጽድቅ ሥራ የተጋን እንሁን፡፡
ኦ ማርያም አንቲ ውእቱ ወላዲተ አምላክ በአማን ወምክሐ ዘመድነ ለኩልነ ሕዝበ ክርስቲያን፣ አዕርጊ ጸሎተነ ቅድመ ገጸ ፍቁር ወልድኪ፣ ለዓለመ ዓለም አሜን።
እመቤታችን ማርያም ሆይ አንቺ በእውነት የአምላክ እናት፣ የባሕርያችን መመኪያ ነሽና ጸሎታችንን በተወደደ ልጅሽ ፊት አሳርጊልን፣ ለዘለዓለሙ አሜን፡፡
ስብሃት ለእግዚአብሔር፣ ወለወላዲቱ ድንግል፣ ወለመስቀሉ ክቡር።