Wednesday 15 February 2017

#አዋጅ_አዋጅ_ያልሰማቹ_ስሙ_በመምህር_ምህረተአብ_አሰፋ ���� ተነሳ ህዝቤ ሆይ ተነሳ መልእክት ስሙ ራሳቹም ጠብቁ ��ለመምህር ምሕረተ አብ አሰፋ የተሰጠ መልስ ወይቤሎ እግዚእ ኢየሱስ አግበኣ ለመጥባሕትከ ውስተ ቤታ እስመ ኲሉ ዘይቀትል በመጥባሕት ይመውት በመጥባሕት ወንጌል ዘማቴዎስ ምዕራፍ ፳፮ ቊጥር ፶፪ በዚያን ጊዜ ኢየሱስ እንዲህ አለው ፦ ሰይፍ የሚያነሡ ሁሉ በሰይፍ ይጠፋሉና ሰይፍህን ወደ ሥፍራው መልስ የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 26 ቊጥር 52 በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን ለመምህር ምሕረተ አብ አሰፋ በቅድሚያ በጌታችንና በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም የከበረውን ሰላምታዬን ላቀርብልህ እወዳለሁ በመቀጠልም ወደ ጉዳዬ ስገባ ሰሞኑን በለቀቅኸው የቪዲዮ መልዕክት ሕዝብን ለዓመፃና ለጥፋት የሚያነሣሣ የክተት ሠራዊት አዋጅ ተገቢ የሆነውን መጽሐፍቅዱዊ ምላሽ ልሰጥህ ስለወደድኩ ይህቺን አጭር መልዕክት እንድትማርበት አዘጋጅቼ አቅርቤልሃለሁና ሳትውል ሳታድር አንብበሃት ከስሕተትህ እንድትመለስ ስል በአክብሮት እጠይቅሃለሁ ሲጀመር በመዝሙርና በቪዲዮ በተቀነባበረ መልኩ የሰዎችን ስም ልታጠፋ ተነሣ ሕዝቤ ተነሣ የጥንቱ እንዳይረሳ ተነሣ ሕዝቤ ተነሣ ስትል ለዓመፃ ሕዝብን የሚያነሣሣ ይህ የምታ ነጋሪት አዋጅ እኔ መምሕር ምህረተ አብ ነኝ ለምትለው ለአንተ ጀብደኛ አድርጎ ያስደነቀህና ለሃይማኖቴ ተቆርቋሪ ስለሆንኩ ነው ይህንን ያደረኩት ያስባለህ ይህ ሥራህ በአባቶች እምነትና በእግዚአብሔር ቃል እውነት ስንመዝነው ፍጹም የወረደ ፣ የዘቀጠ ፣ አላዋቂነትህንና መምህር አሰኝቶ ያስጠራህን ማንነትህን ሳይቀር የተፈታተነ ፣ ያሳነሰህ ፣ ግምት ውስጥም የከተተህ በመሆኑ በእኔ በኩል እጅግ በጣም አዝኜልሃለሁ እንድጸልይልህና ከሰማኸኝም ደግሞ አለፍ አለፍ እያልኩም ቢሆን ዓይኖችህን ሊከፍቱት የሚችሉትን እውነተኛውን የእግዚአብሔርን ቃል እንድነግርህ እንዳስተምርህም ተገድጃለሁ መምህር ምሕረተ አብ በአንተ በኩል አድርጌዋለሁ ትክክል ነኝ የምትለውን አድርገሃል ነገር ግን ከአንተ በፊት ወደነበሩት ወደቀደሙት አባቶች መለስ ብትል እነዚህ አባቶች እንደ አንተ በግብታዊነትና በስሜት እንዲሁ ተነስተው አዋጅ አዋጅ ክተት ሠራዊት ምታ ነጋሪት ሲሉ በሰዎች ላይ የሃይማኖት ጦርነት ለማወጅ አልተነሱም ከአንተ አስተሳሰብ በብዙ የራቁ ፣ የተለዩ ፣ የሰከኑ ፣ ያስተዋሉና የጨመቱ ሆነው ውሃ ከጥሩ ነገር ከሥሩ እንዲሉ ነገርን ከመጀመርያ ከሥሩ አጥንተውና መርምረው ለሚከራከራቸው ሰው መጻሕፍትን ይዘውና ማስረጃ ጠቅሰው ነው የሚነሱት እንግዲህ ከእነዚህ የእምነት አባቶች አንጻር አንተ ይህንን ልትል ከወዴት በቀልክ ? በአባቶች ያላየነውን አጉራ ዘለል ድርጊትህን ፣ ምግባረ ሰናይ ሳይሆን በአባቶች አመክሮ ብሎም በመጻሕፍት እውቀትና ብስለት ያላደገ ፣ ያልተገራ ፣ ያልተቃኘ ፣ መረን የወጣና ምግባረ ብልሹም የሆነ ባሕርይህን አይተናል ስለዚህ እንግዲህ ይቅርታ አድርግልኝ በእኔ በኩል መምሕር ብዬ ልጠራህ በጣም ይቸግረኛል ከመጠምጠም መማር ይቅደም የሚለው የአባቶች አባባል አለና በጣም ተዳፈረኝ ካላልከኝ መምህር የሚለው ማዕረግ የሚበዛብህ ይመስለኛል ለምን ብትለኝ መምህር የሚለው ማዕረግ የሚሰጠው ተምሮና ደቀመዝሙርም ሆኖ በሕይወት ምሳሌነቱም ሳይቀር ሰዎችን ማስተማር ለሚችል የሚሰጥ ነው ነገር ግን መጽሐፍ ያላስተማረውንና አባቶችም ያልወጣቸውን ነገር ሃይማኖቴ በሚል የሞቅታ መንፈስ እንዲሁ ተነሳስቶ ይህንን የተባረከውንና ቅኑን ሕዝባችንን ሃይማኖትህን የሚበርዙ ተነስተውብሃልና ተነሳ ሲሉ ጡሩንባ በመንፋትና የሰዎችንም ስም በከንቱ በማጥፋት በየፌስቡኩና በዩቲዩቡ ላይ ቪዲዮ መልቀቁ በአባቶች እግር ሥር ቁጭ ብለህ ያልተማርክ ፣ ሾልከህም በድንገት ብቅ ያልክና ማይክራፎኑንም በፍጥነት ይዘህ ያልተመዘነ ፣ በአባቶችም በኩል ያላለፈና እነርሱም ያልተስማሙበት ድንገተኛ ወሬ ይዘህ የመጣህና ያወራህ ከዚህም ሌላ ማንንም ሳታስፈቅድ በራስህ ተነሳሽነት እንዲሁ ተነስተህ የተናገርክና የለፈለፍክ አስመስሎብሃል አያያዙን አይተህ ዱላውን ቀማው እንደሚባለውም እንደማስበው ስረዳህ የግዕዙንም ሰዋስው በአግባቡ ያጠናህና ያወቅህ እንኳን አልመሰልከኝም ለነገሩ አንተ ብቻ አይደለህም ብዙ ያለጊዜያቸው የበቀሉ ፣ በቤተክርስቲያኒቱ ስም ተደራጅተውና ማኅበረ እገሌ ሲሉ እራሳቸውን ሰይመው ቤተክርስቲያን ያላላቸውን የሚሉ ፣ ሊቃውንት ያልተናገሩትንና ያላስተማሩትንም በድፍረት የሚናገሩና የሚያስተምሩ ፣ ቤተክርስቲያኒቱም ሳትወክላቸው ራሳቸውን የቤተክርስቲያኒቱ ወኪል አድርገው በመቁጠር ቤተክርስቲያኒቱ እንኳን ልታደርገው ፣ ልታስበው የማትፈልገውን ነገር በጭካኔ ያለ ርህራሄ የሚፈጽሙ ሰዎች እንዳሉ እናውቃለ እነዚህ ሰዎች ለቤተክርስቲያኒቱ ተቆርቋሪ ነን ሲሉ በየአደባባዩና በየጋዜጦቻቸው ሁሉ ይለፍልፉ እንጂ ለአባቶች እንኳ ሳይቀር በሥርዓት የማይታዘዙ ፣ ጉድ እስኪባል ድረስ በዘመናችን ተከብረው ያሉ ብፁዓን አባቶችን ሳይቀር የሚያንጓጥጡና የሚተቹ ፣ ቤተክርስቲያኒቱንም አባት አልባና መሪ አልባ አድርገው ገንጥለው ሊይዙ የሚፈልጉ መሆናቸው በየጊዜው የምንሰማው የአደባባይ ምስጢር ነው ስለዚህ አንተም ሆንክ እንደነዚህ ያሉ ሰዎች መምህርና ሌላም ሌላም ዓይነት ስም ይዘው አዋጅ አዋጅ ሲሉ ላንቃቸው እስኪዘጋ ድረስ በየአደባባዩ ቢያቅራሩና ቢጮኹ የሚሰማቸው የለምና ብዙ አንደነቅም አይገርመንምም ሌላው እንዳልኩህ አንተም ሆንክ እንደነዚህ ዓይነት ሰዎች ይህቺን ቤተክርስቲያን አትወክሉም እንደገናም ሊቃውንቶችዋንና መምህራኖችዋን አትወክሉም ሰው ማንን ይመስላል ቢሉ ውሎውን እንደሚባለው እናንተም ታድያ እንኳን እነርሱ በዋሉበት ልትውሉ ጠረናቸውን እንኳ በአግባቡ ያላሽተታችሁ በመሆናችሁ ነገራችሁ ሁሉ ላም ባልዋለበት ኩበት ለቀማ ሆኗል ወንድሜ ምሕረተ አብ ከዚህም ሌላ አንድ ነገር እንድትረዳ የምፈልገው በቤተክርስቲያኒቱ ውስጥ አድገውና በቅለው ፣ የቤተክርስቲያኒቱንም ትምህርት ለዓመታት ውሻ እየጮኸባቸው አንጀታቸውን አስረውና ተርበው እናንተ ዛሬ ላይ ብቅ ብላችሁ በባዶ ሜዳ እየተንተከተካችሁ ስማቸውን የምታጠፏቸው ሰዎች ባጠገቡ ያልዞራችሁበትንና የማታውቁትን ቅኔውን ፣ ዜማውን ፣ ድጓውን ፣ ጾመ ድጓውን ፣ አቋቋሙን ፣ አራራዩንና ዝማሬ መዋሥዕቱን ፣ የመጻሕፍት ትርጓሜ ብሉያትንና ሐዲሳትን በማወቅ እስከ መምህርነት የደረሱ መምህራን አልፈውም ሄደው በተለያዩ መንፈሳዊ ኮሌጆች በድግሪና በዲፕሎማ ተመርቀው በእግዚአብሔር ቃል እውቀትና ምጥቀት ይህቺን ቤተክርስቲያን ሊያሳድጉና ሊጠቅሙ በየዘመናቱ የተነሱትንና እየተነሱ ያሉትን ምሁራን ጸረ ማርያምና ተሃድሶ ናቸው እያላችሁ ስም በማጥፋት ከዚህም ሌላ ከቅዱስ ሲኖዶስና ከብጹአን አባቶች ጋር በማጣላት ምሁራኑን ከቤተክርስቲያን እንዲባረሩ ታደርጋላችሁ እናንተ የምታምኑትን ትርኪ ምርኪ የሆነውን ነገር ማለትም ቅጠሉን ፣ አመዱን ፣ አጥንቱን ዋሻውንና እንደገናም በዋሻው ውስጥ ተገኝተው በትክክል ማን እንደጻፋቸው እንኳ በውል የማይታወቁ አባት የለሽ የተረት ተረት መጻሕፍቶችን እነዚህ ወገኖች ስላላመኑና ብቸኛ አዳኝ የሆነውን ፣ የኃጢአትም ሥርየት የሚሰጠውን እንደገናም የሰውን ልጆች ሁሉ ወደ አብ መንግሥት ሊያስገባ ብቸኛ መንገድ የሆነውን የድንግል ማርያምን ልጅ ኢየሱስን ስለሰበኩ ብሎም መጽሐፍቅዱሳችን ለሆነው 66ቱ ቅዱሳት መጻሕፍት እውቅና በመስጠት ይህ መጽሐፍ ብቸኛ በእግዚአብሔር መንፈስ የተጻፈ የእግዚአብሔር መጽሐፍ ነው ሲሉ ስላመኑና እርሱንም ብቻ ስላስተማሩ ከቅናትና ከእውቀት ማነስ ተነስታችሁ ምንም በማታውቁት ነገር ለቤተክርስቲያኒቱ ተቆርቋሪ በመምሰል ይህን እውነት ያወቀውንና የተረዳውን ትውልድ ሳይቀር ገጀራና ጎራዴ ይዛችሁ በማስፈራራት ትውልዱን ከሚወዳት ከእናት ቤተክርስቲያኑ ትለያላችሁ እንደገናም ደግሞ ሃይ የሚላችሁ ከልካይ ስላጣችሁ ክተት ሠራዊት ምታ ነጋሪት ስትሉ አዋጅ አወጃችሁ ታድያ እነግርሃለሁ ምሕረተ አብ ይህ መንገድ የሚያዛልቃችሁ አይደለም ለምን ብትል አንተና መሰሎችህ እያደረጋችሁት ያለው ነገር በብዙ ወደ ኋላ የቀራችሁ መሆናችሁን ያሳብቅባችኋልና ነው ምህረተ አብ ወዳጄ ሌላው ልትገነዘባቸው የሚገቡ እውነቶች በቤተክርስቲያኒቱ ውስጥ በቅለው ትምህርቷን በመማር እዚህ በደረሱ የሃይማኖት አባቶች መምህራንና አገልጋዮች እንዲሁም በሥራቸው ያለ ትውልድ ላይ ሰይፍ ልትመዝዝ ይቅርና ሰይፍህን በማንኛውም ፍጥረተ ዓለም ላይ እንድታነሳው መጽሐፍ አይፈቅድልህም ለምን ስትል ፦ 1ኛ )ከላይ በመግቢያዬ ላይ እንደጠቀስኩልህ ሰይፍ የሚያነሡ ሁሉ በሰይፍ ይጠፋሉና ሰይፍህን ወደ ሥፍራው መልስ የሚል የእግዚአብሔር ቃል ተጽፎልሃል የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 26 ቊጥር 52 2ኛ ) በማቴዎስ ወንጌል 5 ፥ 21 _ 23 መሠረት በግዕዙ ቃል እንዲህ ይላል እግረ መንገድህን ከግዕዙ ቃል ጋር እንድትተዋወቅ ብዬ ነው ይህንን የግዕዝ ቃል የምጠቅስልህ ሰማዕክሙ ዘተብህለ ለቀደምትክሙ ኢትቅትል ነፍሰ ወዘሰ ቀተለ ረስሐ ውእቱ ለኩነኔ ወአንሰ እብለክሙ ኩሉ ዘያምዕዕ እኅዋሁ ረስሐ ውእቱ ለኩነኔ ወዘሂ ይቤሎ ለእኁሁ ኅሡር ዘፀርቅ ረስሐ ወይትኴነን በዐውድ ወዘሰ ይቤሎ ዓብድ ረስሐ ውእቱ ወይትኴነን በእሳተ ገሃነም ይላል ይህንን ወደ አማርኛው ስተረጉመው እንዲህ የሚል ነው ለቀደሙት፦ አትግደል እንደ ተባለ ሰምታችኋል፤ የገደለም ሁሉ ፍርድ ይገባዋል እኔ ግን እላችኋለሁ፥ በወንድሙ ላይ የሚቆጣ ሁሉ ፍርድ ይገባዋል፤ ወንድሙንም ጨርቃም የሚለው ሁሉ የሸንጎ ፍርድ ይገባዋል፤ ደንቆሮ የሚለውም ሁሉ የገሃነመ እሳት ፍርድ ይገባዋል የሚል ነው ስለዚህ አይደለም ልንቀትለውም ሆነ ልንገድለው በአንድ ሰው ላይ ሰይፍ ልንመዝዝበት ፣ ገጀራም ልናነሳበት ይቅርና ወንድማችንን ደንቆሮ ጨርቃም ብለን ብንሰድበው እንኳ የገሃነመ እሳት ፍርድ እንደሚገባን እኔ ሳልሆን ይሄ የእግዚአብሔር ቃል ነው የሚናገረው ስለዚህ አንተም ሆንክ አንተን የመሰሉ ሰዎች በዚህ ነገር ውስጥ ተላልፋችሁ የገሃነመ እሳት ፍርድ እንዳይገባችሁ ልትጠነቀቁ ይገባል 3ኛ ) አንተ መንፈሳዊ ሰው ነኝ የምትል ከሆንክና ሌሎች የኔ ተቃራኒዎች የተሳሳቱ ጸረ ቤተክርስቲያንና ተሃድሶዎች ናቸው የምትል ከሆነ መምዘዝ ያለብህ ለሐሜትና ለስድብ ፣ ስምንም ለማጥፋት የተመዘዘ የአንደበት ሰይፍህን አይደለም እንደገናም ጴጥሮስ የገዛ ሰይፉን መዞ የሊቀካህናቱን ባርያ መትቶ ቀኝ ጆሮውን እንደቆረጠው አንተም እንደ ጴጥሮስ የሥጋ ሰይፍ መዘህ የሰው ጆሮ እንድትቆርጥ አይደለም መንፈሳዊ ሰው መንፈሳዊ እንደመሆኑ መጠን የሚመዘው ከነዚህ ከዘረዘርኳቸው ሁሉ የተለየውን ሰይፍ ነው እርሱም የእግዚአብሔር ቃል ነው ለዚህ ነው እንግዲህ ሁሉንም ፈጽማችሁ ለመቆም እንድትችሉ የእግዚአብሔርን ዕቃ ጦር ሁሉ አንሱ ያለን ኤፌሶን 6 ፥ 10 _ 20 ፤ ዕብራውያን 4 ፥ 12 ነገር ግን እነዚህን አንሱ የተባሉትን አንተ ግን እንደሚገባ ማንሳት ስላልቻልክ በጣም ተናደሃል ከዚህም ሌላ የሰው ጆሮ ሊቆርጥ ጴጥሮስ ያነሳውን ገጀራና ለመሳደብ የተዘረጋውን የአንደበትህን ሰይፍ መዝዘሃል ታድያ ከእነዚህ አልባሌ ነገሮች ውስጥ ወጥተህ የቃሉን ሰይፍ እንድትመዝ የሁልጊዜ ጸሎቴ ነው ይሁን እንጂ አንድ ነገር ልልህ የምፈልገው እነዚህ ተሃድሶ የምትላቸው ሰዎች እኔንም ጭምር ማለቴ ነው ሕይወታቸው በቃሉ ስለተለወጠ አንተ እየመዘዝክ ያለውን ሰይፍ እነርሱ ደግሞ የሚመዙት አይደሉም ነገር ግን ከአንተ በበለጠ ሁኔታ በኃይል የታጠቁት የእግዚአብሔር ቃል ሰይፍና በቤተክርስቲያኒቱም ውስጥ በእግዚአብሔር ቃል መሠረት የተጻፈ ፣ ለውጥንም የሚያመጣና ቤተክርስቲያኒቱንም ወደ ጥንተ መሠረቷ የሚመልስ ፣ ከእግዚአብሔር ቃል ጋር የማይጻረር እውነት ስለያዙ እርሱን ደረጃ በደረጃ ቢመዙብህ ፍጹም ልትቋቋማቸው እና በፊታቸውም ልትቆም ያቅትሃል በጴጥሮስ ዘመን እንደነበረው የበዓለ ሃምሳ ስብከት በመንፈስቅዱስ የሆነ የቃሉን ዶፍ ቢያወርዱብህ ደግሞ አንተም ሆንክ በተወደደችው እናት ቤተክርስቲያናችን ኦርቶዶክስ መድረክ ላይ ወዲያና ወዲህ እየተወራጩ ፣ ጭርጭር እያሉም የሚሳደቡ ቢጤዎችሕ ለአፍታም ሳትቆዩ እንደነዛ ሦስት ሺህ ነፍሳት ምን እናድርግ ስትሉ ሙሉ ሕይወታችሁንና እጃችሁን ለዚህ ጌታ እንደምትሰጡ በጣም እርግጠኛ ነኝ ስለዚህ እናንተም የአቅማችሁን ልክ ስለምታውቋት ሆድ ሲያውቅ ዶሮ ማታ ነውና በዚሁ ጉዳይ ላይ እንዲሁ ዳር ዳሩን ፊን ፊን ስትሉ ትሠማላችሁ እንጂ እነዚህን ተሃድሶ ያላችኋቸውን ባልንጀሮች ፊት ለፊት ልትቋቋሙ የምትችሉበት መንፈሳዊ ብቃትም ሆነ እውቀቱን ገና ያልገበያችሁ በመሆናችሁ በበዛ ፍርሃት ውስጥ ትሆናላች እንጂ በአጠገባቸው ዝር አትሉም የሐዋርያት ሥራ ምዕራፍ 7 ፥ 8 _ 15 ፣ 1ኛ ጴጥሮስ 2 ፥ 1 _ 3 ን አንብቡት መልዕክቴን ስጠቀልል ወንድሜ ምሕረተ አብ አሰፋ በዚህ መልዕክት ከነጓደኞችህ በብዙ እንደምትጠቀሙ ተስፋ አደርጋለሁ ጥያቄ ካለህ ጠይቀኝ እኔም ከዚህ በኋላ ወደ እውነቱ እንድትመጣ የእግዚአብሔርን ቃል በመናገር እከታተልሃለሁ እጸልይልሃለሁ የአባቶቻችን አምላክ የውስጥ ዓይኖችህን ያብራ ተባረክ ሰላም ሁን ከ JOSHUA BREAKTHROUGH RENEWAL APOSTOLIC MINISRRY ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን ቀሲስ አባ ዮናስ ጌታነህ

No comments:

Post a Comment