Friday 12 February 2016

ክፍል ሁለት የመልዕክት ርዕስ ፦ የሰዎችን ሥራም ሆነ የሥራ ጅማሬን ማወቅ

2 Samuel 13 Amnon and Tamar
 Juda and Jesus



 ክፍል ሁለት


የመልዕክት ርዕስ ፦

የሰዎችን ሥራም ሆነ የሥራ ጅማሬን ማወቅ



እርሱም ቍራሹን ከተቀበለ በኋላ ወዲያው ወጣ፤ ሌሊትም ነበረ   የዮሐንስ ወንጌል 13 30





በክፍል አንድ መልዕክቴ ላይ የደሊላን የሥራ ጅማሬ ያላወቀው ሶምሶን የወደደችውና ከእርሱም ጋር የሆነች መስሎት እንዴት ባለ ውድቀት ውስጥ ተላልፎ እንደተሰጠ በሰፊው ተማምረንበታል ደሊላ ግን ሥራዋን አንድ ብላ የጀመረችው ኃይሉ ከእርሱ በሄደ ጊዜ ስለሆነ ልታዋርደውም ጀመረች እያለ የክፍሉ ሃሳብ ይናገራልና በእነዚህና በመሳሰሉት ዙርያ ነበር በስፋት የተነጋገርነው የክፍል ሁለት መልዕክቴም ከዚሁ የቀጠለ ነው በክፍል ሁለት መልዕክት የምናየው የተቀባው መሲሃችን ኢየሱስን ነው ጌታችን ኢየሱስ የሰዎችን ሥራም ሆነ የሥራ ጅማሬን በትክክል የሚያውቅ ነው በመሆኑም ኢየሱስም ከፋሲካ በዓል በፊት፥ ከዚህ ዓለም ወደ አብ የሚሄድበት ሰዓት እንደ ደረሰ አውቆ፥ በዚህ ዓለም ያሉትን ወገኖቹን የወደዳቸውን እስከ መጨረሻ ወደዳቸው ይለናል የዮሐንስ ወንጌል 13 1 ይሁን እንጂ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ፍቅር በምክንያት ያልሆነና እንዲሁ የሆነ ፍቅር በመሆኑ ከማንም ጋር ልናነጻጽረውም ሆነ ልናወዳድረው አንችልም እንደገናም በሁኔታዎች የማይለዋወጥ ገደብ የሌለውና እስከመጨረሻውም የሆነ ፍቅር ነው ለዚህም ነው ሐዋርያውና ወንድማችን የሆነው ጳውሎስ በመንፈሱ በውስጥ ሰውነታችሁ በኃይል እንድትጠነክሩ ክርስቶስም በልባችሁ በእምነት እንዲኖር እንደ ክብሩ ባለ ጠግነት መጠን ይስጣችሁ፤ የእናንተ ሥርና መሠረት በፍቅር ይጸና ዘንድ፥ ከቅዱሳን ሁሉ ጋር ስፋቱና ርዝመቱ ከፍታውም ጥልቅነቱም ምን ያህል መሆኑን ለማስተዋል፥ ከመታወቅም የሚያልፈውን የክርስቶስን ፍቅር ለማወቅ ትበረቱ ዘንድ፥ እስከ እግዚአብሔርም ፍጹም ሙላት ደርሳችሁ ትሞሉ ዘንድ ያለን ኤፌሶን 3 16 _ 19 ስለዚህ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ፍቅር እንወቅህ ብንለው እንኳ አውቀነው የማንጨርሰው ፍቅር ልናውቀውም የማንችለውና ከመታወቅም የሚያልፍ ፍቅር ነው የፍቅሩ ልክ ደግሞ  ፍጹም የሆነ የእግዚአብሔር የሙላቱን መጨረሻ  የሚገልጽ ነው ታድያ ይሄ ደቀመዛሙርቱን እስከመጨረሻው የወደደ ከክርስቶስ የወጣ ፍቅር ዝም ብሎና ተራ በሆነ ወረታዊ የመንደር ፍቅር ዓይነት  እውር ሆኖ  አበድኩልህ ከነፍኩልህ ስለዚህ ምኔን ልስጥህ የሚል ሰዋዊ ተቀያያሪ ሶምሶናዊም ሆነ አምኖናዊ ዓይነት ፍቅር አይደለም 2 ሳሙኤል 13 1 _ 15 መሣፍንት 14 1 _ 4 10 _ 20 መሣፍንት 16 1 _ 22 ይሄ ፍቅር እስከመጨረሻው የወደደና የሚወድ የክርስቶስ ፍቅር ሲሆን ነፍስን እስከመስጠት ድረስ የወደደም ፍቅር ነው የዮሐንስ ወንጌል 15 13 በዚያው መጠን ደግሞ አሳልፎ የሚሰጠውንና የሚክደውንም ጭምር የሚያውቅ  ነው የዮሐንስ ወንጌል 13 11 36 _ 38 ወገኖቼ ታድያ ይህ የክርስቶስ ፍቅር ምንም እንኳ እስከመጨረሻው የሚወድ ፍቅር እና  ነፍስንም እስከመስጠት ድረስ የወደደ ፍቅር ቢሆንም ማየት   ማጣራትና መለየትም የሚችል ፍቅር በመሆኑ እስከመጨረሻው ይውደድ እንጂ ሁሉንም አይቶ አጣርቶና ለይቶ ያውቃል ይህ ማለት ደግሞ የሚሸጠውንም ሆነ የሚክደውን ለይቶ ያውቃል ማለቴ ነው ለእኛም እንዲህ ሊሆንልን ይገባል የተወደዳችሁ ቅዱሳን ዛሬ በዘመናችን መንፈሳዊ በሚመስል እህታዊና ወንድማዊ የፍቅር የአገልግሎት የአብሮነትና የመሳሰሉት ግንኙነቶች  ጀርባ አስተውለን አጢነንና ተጠንቅቀንም ጭምር ካልተመላለስን  ወዳልተፈለገ የግንኙነት መስመር ውስጥ በመግባት የጌታን ስም እስከማሰደብ ልንደርስ እንችላለን ግንኙነቶች ሁሉ መንፈሳዊ ስለሆኑና መንፈሳዊም ግንኙነቶች ናቸው ስለተባሉ ሙሉ የሆነ አመኔታን ሰጥተን መልካምና ጥሩ ናቸው ልንል አንችልም ቅድስናን ንጽሕናን የተሞሉ ፍርሃተ እግዚአብሔርንም ገንዘብ ያደረጉ  ግንኙነቶች ካልሆኑ ፍጻሜያቸው መንፈሳዊና ክርስቶሳዊ ፍቅር መሆኑ ቀርቶ ይሁዳዊ ፣ ደሊላዊና አምኖናዊ  ፍቅር ይሆኑና  የአምላካችንን ስም የሚያሰድቡ ብቻ ሳይሆኑ የክርስቶስ  ቤተክርስቲያንን ሳይቀር አንገት የሚያስደፉ ይሆናሉ ስለዚህ በግንኙነቶቻችን ዙርያ በብዙ ልናስብበትና ጥንቃቄም ልናደርግ ይገባል ግንኙነቶቻችንንም እንደ እግዚአብሔር ቃል በሆነ የግንኙነት መንገድ ልናስኬደው ፣ ልናስተካክለውም ያስፈልጋል መጽሐፋችን ለርኩሰት ሳይሆን እግዚአብሔር በቅድስና ጠርቶናልና ነው የሚለን 1 ተሰሎንቄ 4 3 _ 8 ቅድስና ዋነኛውና ቀዳሚው የእግዚአብሔር ጥሪ ፣ የእግዚአብሔርም ፈቃድ ነው ስለዚህ  ደግሞ እኛም ልንፈልገው ይገባል ያለእርሱ እግዚአብሔርን ማየት አንችልምና ዕብራውያን 12 14 ቅድስና ከሌለ  አገልግሎት አብሮነት፣ ኅብረት ግንኙነትም ሆነ መሰባሰብ ሌላም ሌላም መንፈሳዊ ተግባሮችን  ያካተቱ ናቸው የምንላቸው ነገሮች ሁሉ የሉም ስለዚህ ቅድስና በሕይወታችን ቀዳሚውን ቦታ ሊይዝ ይገባል እንደገናም በዕብራውያን 10 23 _ 25 ላይ የተስፋን ቃል የሰጠው የታመነ ነውና እንዳይነቃነቅ የተስፋችንን ምስክርነት እንጠብቅ ለፍቅርና ለመልካምም ሥራ እንድንነቃቃ እርስ በርሳችን እንተያይ በአንዳንዶችም ዘንድ ልማድ እንደ ሆነው፥ መሰብሰባችንን አንተው እርስ በርሳችን እንመካከር እንጂ፤ ይልቁንም ቀኑ ሲቀርብ እያያችሁ አብልጣችሁ ይህን አድርጉ ይለናል ወገኖቼ የተስፋውን  ምስክርነት የሚጠብቅ ለፍቅርና ለመልካም ሥራ የተነቃቃ ነው መሰባሰቡን አይተውም ይመካከራል ይተያያል ቀን ሲቀርብ እያየም ዝም ብሎና እጁን አጣጥፎ በግዴለሽነት አይቀመጥም የሃላፊነቱን ድርሻም ለመወጣት አብልጦ ይህንን ያደርጋል ታድያ እነዚህ ነገሮች ሁሉ በመልካም ሁኔታ በሕይወታችን እንዲካሄዱና እንዲጠናቀቁ የሚያስችል የተስፋን ምስክርነት መጠበቅ ነው ጌታ እግዚአብሔርም የተስፋን ቃል የሰጠና የታመነ ስለሆነ ከእኛ የተስፋን ምስክርነት መጠበቃችንን በብዙ ይፈልገዋል የተስፋን ምስክርነት መጠበቅ ከሌለ ግን እግዚአብሔር የሰጠው የተስፋ ቃል ቢኖርም  ለእኛ ግን እግዚአብሔር  ሰጠን የምንለው የተስፋ ቃል አይኖረንም ፣ ለፍቅርም ሆነ ለመልካም ሥራ መነቃቃት ፣ መሰባሰብ መመካከር ፣ መተያየት የሚባሉ ነገሮች  ሁሉ አይታሰቡም   የተስፋችንን ምስክርነት መጠበቅ  እነዚህን ሁሉ ነገሮች ለማከናወንና ለመፈጸም ዋነኛ ነገር ነው ቅዱሳን ወገኖቼ እንግዲህ በምልልሳችንም ዙርያ እንዴት እንድንመላለስ በጥንቃቄ መጠበቅ አለብን  ኤፌሶን 5 15 _ 20 ዘመኑም ይህንን የእግዚአብሔር ቃልና የእግዚአብሔር እውነት ለብሰን እንድንራመድ የሚገፋን   ስለሆነም ለእነዚህ ከእግዚአብሔር ለተሰጡን መለኮታዊ የእግዚአብሔር ቃል እውነቶች  መፈጸም ራሳችንን  በዚሁ በእግዚአብሔር ቃል ማዘጋጀትና ማሳደግ አለብን ኢየሱስ ጌታችን እስከመጨረሻው በሚወድ ፍቅር ውስጥ ቢሆንም የሚሸጠውንም ሆነ የሚክደውን ያውቃልና  ይሁዳን እንዲህ አለው እንግዲህ የምታደርገውን ቶሎ ብለህ አድርግ አለው ነገር ግን ከተቀመጡት ስለ ምን ይህን እንዳለው ማንም አላወቀም ይሁዳ ከረጢቱን የያዘ ስለ ሆነ፥ ኢየሱስ፦ ለበዓሉ የሚያስፈልገንን ግዛ፥ ወይም ለድሆች ምጽዋት እንዲሰጥ ያለው ለአንዳንዱ መስሎአቸው ነበርና እርሱም ቍራሹን ከተቀበለ በኋላ ወዲያው ወጣ፤ ሌሊትም ነበረ  ይለናል ስለዚህ ኢየሱስ ይሁዳን ያወቀው ገና ሌሊት ሳለ ቁራሽ ሲሰጠው ነው ታድያ ጌታችን ኢየሱስ ይሁዳን ሊያውቀው ሌሊቱ አልነጋበትም ወይም አልረፈደበትም ሶምሶን ደሊላን ሊያውቃት ጊዜው ረፍዶበት ነበር ኢየሱስ ግን ይሁዳን ያወቀው ገና ሌሊት ሳለና ቁራሽ ሲሰጠው ነው ይሁዳም ከዚያ በኋላ ከኢየሱስ ጋር ብዙ መጓዝ አልቻለም ለዚህም ነው እንግዲህ እርሱም ቍራሹን ከተቀበለ በኋላ ወዲያው ወጣ፤ ሌሊትም ነበረ የሚለን ዮሐንስ 13 21 _ 30  ደሊላ ግን ከሶምሶን ጋር እውነት በሚመስል የሽንገላ ፍቅር  በብዙ ተጉዛለች አብራም በልታለች ጠጥታለች መብላት መጠጣት ብቻ አይደለም ከዚህም አልፋ አጠጥታና ጠጥታ አስክራለች ተሳክራለች  ጸጉርም አስላጭታ የዚሁ የሶምሶንን ጸጋ አስወስዳለች ልታዋርደውም ጀምራና ጨርሳ  በፍልስጥኤማውያን በኩል የተሰጣትን ተልዕኮ በሶምሶን ላይ  ሙሉ  ለሙሉ አሳክታለች ለይሁዳ ግን ይሄ ሁሉ አልሆነም ይሁዳ የታወቀበት ገና በሌሊቱ ቁራሽ ከተቀበለ በኋላ ስለነበረ በዚያው ሌሊት ይሁዳ ወጣ ስለዚህም  ኢየሱስ እንዲህ አለ አሁን የሰው ልጅ ከበረ እግዚአብሔርም ስለ እርሱ ከበረ እግዚአብሔር ስለ እርሱ የከበረ ከሆነ፥ እግዚአብሔር ደግሞ እርሱን ራሱን ያከብረዋል ወዲያውም ያከብረዋል አለ  እንግዲህ ይህ ይሁዳ ቁራሽ ተቀብሎ የወጣበት ሌሊት ለኢየሱስ የመክበር ሌሊት ነበር እንደገናም ኢየሱስ ብቻ ሳይሆን አባቱ እግዚአብሔርም ሳይቀር የከበረበት ሌሊት ነበር ይሁዳ ማንም ሳያውቅብኝ በሚደብቀኝ ሌሊት ውስጥ ሆኜ ኢየሱስን አሳልፌ አሰጣለሁ ያለበት ሌሊት ለኢየሱስም ሆነ ለአባቱ ለእግዚአብሔር የመክበር ሌሊት ሆነ ታድያ ሌሊቱ ሌሊት ሆኖ የቀረው ለይሁዳ ነው ለኢየሱስ ግን ጨለማ በእርሱ ዘንድ ከቶ የለምና ሌሊቱ ሌሊት ቢሆንም ኢየሱስ  ከአባቱ ጋር ሆኖ  መክበሩን ያወቀበት   ያረጋገጠበትም ሌሊት ሆኖለታል   1 ዮሐንስ 1 ታድያ ይሄ ሁሉ የይሁዳ ሁኔታ ለደቀመዛሙርቱ ግልጽ ሳይሆን ቀርቶ ግር እንዲላቸው የሆነበት  ጉዳይ ቢሆንም  ለኢየሱስ ግን የታወቀና የተረጋገጠ የመክበርያ ጊዜ ነበረ ወገኖቼ ይህ ነው እንግዲህ የሥራን ጅማሬ ማውቅ የይሁዳ የሥራ ጅማሬ ሳይውል ሳያድር በዚያው ሌሊት በራሱ በኢየሱስ የታወቀ ሆኖ ነበረ ከጌታችን ከኢየሱስ ሊሰወር የሚችል አንዳች ነገር የለምና እንደውም ኢየሱስ በዚህ ጉዳይ ላይ አንድ ነገር ብሎ ነበር እርሱም ምንድነው ስንል   የሰው ልጅስ ስለ እርሱ እንደ ተጻፈ ይሄዳል፤ ነገር ግን የሰው ልጅ አልፎ ለሚሰጥበት ለዚያ ሰው ወዮለት፤ ሰው ባልተወለደ ይሻለው ነበር አላቸው ይለናል ከዚህም ሌላ እኔ እናንተን አሥራ ሁለታችሁን የመረጥኋችሁ አይደለምን ?  ከእናንተም አንዱ ዲያብሎስ ነው ብሎ መልሶላቸውም ነበር  የማርቆስ ወንጌል 14 21 የማቴዎስ ወንጌል 26 24 የሉቃስ ወንጌል 20 21 _ 23 የዮሐንስ ወንጌል 6 70 ስለዚህ ኢየሱስ ባላወቃት በይሁዳ ተንኮል ተጠላልፎና ተላልፎ የተሰጠ ሳይሆን ከይሁዳ ይልቅ የይሁዳን ተንኮል በብዙ ያወቀ ስለሆነ እንደ ይሁዳ ተንኮል ሳይሆን እንደተጻፈለት የሄደ ነው ለዚህም ነው በይሁዳ ላይ ይህንን  አሳዛኝ ነገር የተናገረው ወገኖቼ እኛም ታድያ መንፈሳውያን ስንሆን እንደዚሁ ነን እኛ ሁሉን እንመረምራለን እንጂ እኛ ግን በማንም አንመረመርም 1 ቆሮንቶስ 2 15 ውድ የቃሉ እና የበረከቱ ተካፋዮች ቅዱሳን ወገኖቼ ሆይ ጌታ እግዚአብሔር በምናነበው ቃል ሁላችንንም ይጥቀመን እነዚህን ሁለት ተከታታይ የሆኑ መልእክቶችን ተጠቀሙበት   እላችኋለሁ ጌታ እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ይባርካችሁ በማለት የምሰናበታችሁ


Joshua Breakthrough Renewal Teaching and Preaching Ministry አገልጋይና ባለ ራዕይ

ቀሲስ ዮናስ ጌታነህ  ነኝ

God bless u all People of God

Amen and Amen

No comments:

Post a Comment